Friday, July 5, 2013

በኢትዮዽያ ‹‹ግብረ ሰዶማዊነት›› ስር ሰዷል – (ከዳንኤል ክብረት)

ወዳጆቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት!?
አሁን ያለንበት ወቅት አብዛኞቹ ትምህርት ቤቶች ተዘግተው ልጆቻችን ቤት ውስጥ መዋል የጀመሩበት፣ ወይም የክረምት መክረሚያ ነገሮችን ማከናወን የጀመሩበት ጊዜ ነው፡፡ በበጋ ከነበረው የወላጆች ወከባ ዐረፍ ብለናል፡፡ ልጆችን ትምህርት ቤት ማድረስ፣ የቤት ሥራ ማሠራት፣ ግዙ፣ አምጡ፣ ኑ፣ ሂዱ ከሚሉ የትምህርት ቤቶች ትእዛዞች ዐረፍ ያልንበት ሰሞን ነው፡፡ አሁን ልጆቻችንን ስለሚመለከቱ ሌሎች ጉዳዮች ለመነጋገር ምቹ ጊዜ ነው፡፡ እኔ ሁለት ጉዳዮችን መርጫለሁ፤ ዛሬ አንደኛውን እናንሣው፡፡
ጉዳይ አንድ
ባለፈው ሰሞን አንዲት እናት ወደ ቢሮዬ መጥተው እንዲህ አወጉኝ፡፡ ‹‹ልጄ የአሥራ ሁለት ዓመት ልጅና የ 5ኛ ክፍል ተማሪ ነው፡፡ አልፎ አልፎ የማይበት ጠባይ ግራ የሚያጋባኝ እየሆነ ተቸግሬ ነበር፡፡ ወደ ትምህርት ቤት ሲሄድ የእኔን ሽቱ ይቀባል፡፡ እኔም ይህን ሳይ የልጅ ነገር አድርጌ ትቼው ነበር፡፡ በኋላ ግን ከሌላው ነገር ጋር ሲደረብብኝ ነው ግራ የተጋባሁት፡፡ ፀጉሩን እንደ ሴቶች ማስተኛት ይፈልጋል፡፡ ጥብቅ ያለ ሱሪ ካልገዛሽልኝ ይለኛል፡፡ አንድ ቀን ትምህርት ቤት አድርሼው መኪናዬን አዙሬ ልመለስ ስል ከኋላ ያለውን መኪና እንዳልነካው ዞር አልኩ፡፡ ያን ጊዜ ያየሁትን ነገር ዓይኔ ሊያምን አልቻለም ነበር፡፡ ከአንድ ሌላ ወንድ ልጅ ጋር ከንፈር ለከንፈር ሲሳሳሙ አየኋቸው፡፡ ከኋላዬ የነበረው መኪና በጡሩንባ እየጮኸብኝ እንኳን የማየውን ተጠራጥሬ ለረዥም ሰዓት ፈዝዤ ነበር፡፡
ሥራ ከገባሁ በኋላ እጅግ ፈዝዤ ነበር፡፡ የቢሮ ሰዎች ሁሉ እየደጋገሙ ምን እንደሆንኩ ይጠይቁኝ ነበር፡፡ ግን ለማን ምን ብዬ ልንገረው? ነገሩ እጅግ አሳፋሪ ነው የሆነብኝ፡፡ ቢቸግረኝ ወደ አንዲት ጓደኛዬ ባለቤት ጋር ደወልኩ፡፡ እርሱ ሐኪም ነበርና ምናልባት ከረዳኝ ብዬ አሰብኩ፡፡ በስልክ አነጋገሬ አደጋ የደረሰብኝ ይመስል ስለነበር እየከነፈ ቢሮዬ መጣ፡፡ ከእርሱ ጋር ተያይዘን ወጣንና አንድ ቦታ ቁጭ አልን፡፡ በልጄ ላይ ያየሁትን ነገር ሁሉ ነገርኩት፡፡ እርሱም ከሌሎች የሰማቸውን የባሱ ነገሮች እየነገረ አጽናናኝ፡፡ ከዚያም የበለጠ ርግጠኛ ለመሆንና ችግሩንም በሚገባ ለመረዳት ልጄ በማይኖርበት ሰዓት የልጄን ዕቃዎች እንድፈትሻቸው ነገረኝ፡፡ አንድ ቀን አባቱ ወደ መዝናኛ ቦታ እንዲወስደው ነገርኩትና እኔ ዕቃዎቹን መፈተሽ ጀመርኩ፡፡ ያኔ ነው የልጄን ጉዳይ በጥልቀት የተረዳሁት፡፡ እኔ ያልገዛሁለት አንድ ቀይ ቲሸርት አገኘሁ፡፡ ቲሸርቱ ላይ በእንግሊዝኛ ‹I am a gay› የሚልተጽፎበታል፡፡ ዕንባዬን መቆጣጠር አልቻልኩም፡፡ አልጋው ላይ ተቀምጬ ለረዥም ጊዜ አለቀስኩ፡፡ ከዚያ በኋላ መቀጠል አልቻልኩም፡፡ ልጄን እንዳጣሁት ገባኝ፤ ልጄን እንደማላውቀው ገባኝ፤ ልጄና እኔ በተለያዩ መንገዶች እየተጓዝን መሆኑ ገባኝ፡፡
የጓደኛዬ ባለቤት በጉዳዩ ላይ እንዴት ከልጄ ጋር ልወያይ እንደምችል መንገዶችን አመላከተኝ፡፡ አንድ ቀን ከልጄ ጋር ከአዲስ አበባ ወጣ አልን፡፡ አብሬው ስጫወት ዋልኩና ለሻሂ ዐረፍ ስንል አንድ ስልክ አነሣሁ፡፡
እንደ ደነገጠ ሰው ሆኜ ነበር የማወራው፡፡ ልጄም ድምፄን እየሰማና ሁኔታዬን እያየ ተደናገጠ፡፡ ስጨርስ ምን እንደሆንኩ ጠየቀኝ፡፡ ‹‹አንዲት ጓደኛዬ ከባድ ነገር እንደ ደረሰባት፡፡ ልጇ ግብረ ሰዶማዊ እንደሆነባት፡፡ በዚህም ምክንያት በሕግ ሊጠየቅ መሆኑን›› ነገርኩት፡፡ እጅግ ደነገጠ፡፡ ‹‹የእኔ ልጅ መቼም እንዲህ ያለ ነገር አያደርግም›› ብዬ ተውኩት፡፡ አፍጥጦ ዓይን ዓይኔን ያየኝ ነበር፡፡ ‹‹በጣም ከባድ ነገር ነው የገጠማት፤ ግብረ ሰዶማዊ ማለትኮ በሃይማኖታችንም ትክክል አይደለም፤ እግዚአብሔር ግብረ ሰዶማውያንን አጥፍቷቸዋል፡፡ ከዚያም በላይ ግብረ ሰዶማውያን በኅሊናቸውም ሆነ በማኅበራዊ ኑሮአቸው ላይ ችግር እንደሚገጥማቸው፤ ከሕዝቡም እንደሚገለሉ፤ አኗኗራቸውም ከተፈጥሮ ሕግ ውጭ እንደሆነ፤ ወንድ ከሴት ጋር ሴትም ከወንድ ጋር እንጂ ወንድ ከወንድ፣ ሴትም ከሴትጋር የሚደረገው ግንኙነት እንስሳት እንኳን የማይፈጽሙት መሆኑን፡፡ የወሲብ ግንኙነት ማንኛውም ወንድ ከ ተፈቀደለት ሴት ጋር ብቻ፣ ባህሉና እምነቱ፣ ሕጉም በሚፈቅደው እድሜና ሁኔታ የሚፈጸም መሆኑን›› እየዘረዘርኩ መግለጥ ጀመርኩ፡፡ ዝም ብሎ ነበር የሚያዳምጠኝ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ልጆቻቸውን ግብረ ሰዶማውያን እንደሚያደርጓቸው፤ እነዚህ ልጆችም ሌሎችን ልጆች አባብለው ወደዚህ እንደሚያስገቧቸው፤ እንዲያውም ‹I am a gay› የሚል ልብስ የሚለብሱ እንዳሉ ነገርኩት፡፡
ግራ ሳይገባው አልቀረም፡፡ ስለ እርሱ እንደምናገር ገምቷል፡፡ ስጨርስ ‹‹የኔ ልጅ አንተ ግን እንደዚህ አታደርግም አይደል?›› አልኩት፡፡ ምንም አላለኝም፡፡ ዝም አለኝ፡፡ መሬት መሬት ያይ ጀመር፡፡ ‹‹ምነው የኔ ልጅ ችግር አለ እንዴ›› አልኩት፡፡ ዝም አለ፡፡ ‹‹አደራህን አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ያሉ ልጆች ሌሎች ልጆችን ሳያውቁት ወደዚህ ነገር እያስገቧቸው ነውና ተጠንቀቅ›› አልኩት፡፡ እሺምእምቢም አላለኝም፡፡ ‹‹አንተ ይህንን ስታደርግ ካየሁ፤ እኔ ወዲያው ነው የምሞተው›› ስለው ተስፈንጥሮ መጥቶ ጭኔ ላይ ተደፋ፡፡ ሲያለቅስ ይሰማኛል፡፡ ዕንባውም እግሬን ሲያሞቀው ይታወቀኛል፡፡ እኔም እያለቀስኩ ነበር፡፡ ከብዙ የዝምታ ልቅሶ በኋላ ‹‹እማዬ እኔኮ ጌይ ሆኛለሁ›› አለኝ፡፡ ቀድሜ ባውቅም ያ ሰዓት ግን መብረቅ የመታኝ ነበር የመሰለኝ፡፡ ከልጄ አንደበት ይህንን ስሰማ ኩምሽሽ ብዬ ትንሽ የሆንኩ መሰለኝ፡፡ የማደርገው ጨነቀኝ፤ ምን ልመልስለት? ምንልበለው? ግራ ተጋባሁ፡፡ ‹‹ለምን ልጄ? ለምን?›› አልኩት፡፡ ከእኛ ራቅ ብለው የሚያዩን ሰዎች ሁኔታዬ ግራ አጋብቷቸው ሁሉም እኔን ያያሉ፡፡
‹‹እኛ ትምህርት ቤትኮ ብዙ ልጆች አሉ›› አለኝ፡፡
‹‹ምን ምን ታደርጋላችሁ?›› አልኩት
‹‹ሽቱ ተቀብተው ይመጣሉ፤ ደግሞ አንድ ዓይነት ማስቲካ ነው የምንበላው፤ ‹I ama gay› የሚል ቲሸርት እንለብሳለን›› አለኝ፡፡
‹‹ቲሸርቱን ማን ነው የሰጣችሁ?›› አልኩት
‹‹አንድ ልጅ ነው ያመጣልን፤ ለሁላችን ሰጠን፡፡ ግን ከዩኒፎርማችን ሥር እንድንለብሰው ነግሮናል››
‹‹ሌላስ?››
‹‹ደግሞ አንድ ልጅ የጌይ ፊልም በዕረፍት ጊዜ ያሳየናል››
‹‹የት ነው የሚያሳያችሁ?›› ‹‹በኪሱ የሚያመጣው ሞባይል አለ፡፡ እናቴ ናት የምትጭንልኝ ብሏል››
የምሰማውን እንዴት ልመነው?
‹‹እርሱኮ [የልጁን ስም እየነገረኝ] አባቱ ትምህርት ቤት ሲሸኘው ሁልጊዜ ከንፈሩን ይስመዋል›› አለኝ፡፡ ይኼኔ ነቃሁ፡፡ አስታወስኩ፡፡ ሰውዬውንም ዐወቅኩት፡፡ እኔም ደስ አይለኝም ነበር፡፡ አባት ወንድ ልጁን፣ እናትም ሴት ልጇን ከንፈራቸውን መሳም እዚህ ትምህርት ቤት የማየው ነገር ነው፡፡ ይህ ነገር ልጆቻችን ይህንን መሰሉን ተግባር ከዕድሜ ቀድመው እንዲለምዱት ያደርጋል፡፡ ከዚያም አልፎ ነገ ሌሎች ግብረ ሰዶማውያን በልጆቹ ላይ ይህንን መሰል ተግባር ሲፈጽሙባቸው ምንም እንዳይመስላቸውና የፍቅር መግለጫ አድርገው እንዲወስዱት ያደርጋቸዋል፡፡ ከባህላችን ያፈነገጡ ነገሮችን በልጆቻችን ላይ ማድረግ እነዚህ ነገሮች በልጆቻችን ላይ በሌሎች አካላት ሲደረጉባቸው እንዳያስተውሉት እንዳይጸየፉትም ያደርጋቸዋል፡፡
‹‹ለመሆኑ አብራችሁ ስትሆኑ ምን ታደርጋላችሁ?›› አልኩት፡፡
‹‹አንዳንድ ወንዶች ልጆች ይሳሳማሉ፤ እኔ ግን ይደብረኛል፤ ደግሞ ይተሻሻሉ›› አለኝ፡፡ ከገጽታው የመቅፈፍ ስሜት አየሁበት፡፡ ይህንን ስሜት ስመለከት ወደ ችግሩ ውስጥ ዘልቆ እንዳልገባበት ተረዳሁ፡፡ እኔ የማዝነው በባህላችን ተከብሮ የኖረውን የወንድም ለወንድም፣ የእኅት ለእኅት ግንኙነት ግብረ ሰዶማዊነት እያጠፋብን በመሆኑ ነው፡፡ እኔ ከአክስቶቼ ልጆች ጋር አብሬ እየተጫወትኩ፣ አብሬእየተኛሁ ነው ያደግኩት፡፡ ልጆቻችን ግን እንዲህ ማድረግ ላይችሉ ነው፡፡ ከአጎታችን፣ ከአክስታችን ጋር መተኛት ለኛ ደስታችን ነበር፡፡ ዛሬ ግን ዘመዶች በዘመዶች ላይ እንዲህ የሚፈጽሙ ከሆነ ዝምድናችን ሊጠፋብን ነው፡፡ መምህሮቻችንን፣ የሃይማኖት አባቶችን፣ የቤት ሠራተኞችን፣ የጥበቃ ሠራተኞችን እየተጠራጠርን ልንኖር ነው፡፡ ግብረ ሰዶምነት ባህላችንን እጅግ አድርጎ ነው የሚያበላሸው፤ ማኅበራዊ ግንኙነቶቻችንን ነው የሚበጣጥሰው፤ እንዴት ያለ ችግር ውስጥ ነው የገባነው በእግዚአብሔር? በኋላ ከአንዳንድ የሕክምና ባለሞያዎች ጋር ስንነጋገር ብዙ ነገር ሰማሁ፡፡ በከተማችን ውስጥ የግብረ ሰዶማውያን ማዘውተሪያዎች የታወቁ ናቸው፡፡ የራሳቸው የመግባቢያ ‹ቋንቋም› አላቸው፡፡ ትልልቆቹ ግብረ ሰዶማውያን ድራግ በመውሰድ ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ እጅግ የሚያሳዝነው ደግሞ ለሕፃናቱ ድራጉን በከረሚላ መልክ ይሰጧቸዋል፡፡ ከወላጆቻቸው ለመደበቅ ሲሉ ልጆቹ ግለኛነትን ይመርጣሉ፡፡ ከሌሎች ልጆች ወይም ከዘመዶቻቸው ጋር ከመጨዋት ይልቅ ከጌምና ከቴሌቭዥን ጋር ብቻ መሆንን ይፈልጋሉ፡፡ በተለይም ፌስ ቡክን በሚገባ ለዚህ አስተሳሰብ ማራመጃ ይጠቀሙበታል፡፡ ወላጆች ኢንተርኔትን ልጆቻችን ያለእድሜያቸው እንዳይጠቀሙበት ማድረግ አለብን፡፡ ስለ ኢንተርኔት አጠቃቀም፣ ስለ ጥቅምና ጉዳቱ ሳንነግራቸው ነው የምንፈቅድላቸው፡፡ ይኼኔ ከበጎው ይልቅ ክፉውን የመያዝ ዕድላቸው ይሰፋል፡፡ በቤታችን ውስጥ ያስገባናቸውን የቴሌቭዥን ቻነሎችንም መቆጣጠር አለብን፡፡ ልጆቻችን ክፉውንም ደጉንም ዝም ብለው እንዲያዩ ማድረግ የለብንም፡፡ ግብረ ሰዶምን የሚያበረታቱ ቻነሎች አሉ፡፡
‹አሁን ልጅዎ ከችግሩ በሚገባ ወጥቶልዎታል?›› አልኳቸው፡፡
‹‹ሙሉ በሙሉ ከችግሩ ወጥቷል ማለት አልችልም፤ አሁንም እጠራጠራለሁ፡፡ ፍርሃቱ ገና አልለቀቀኝም፡፡ ነገር ግን ክትትሌን አላቆምኩም፤ ከልጄ ጋር ያለኝን ቀረቤታም ጨምሬያለሁ፤ ስለ ብዙ ነገሮችም እንነጋገራለን፤ የሃይማኖት ትምህርት እንዲማርም እያደረግኩ ነው፡፡ አንድ የማውቀው የሥነ ልቡና ባለሞያ ስለ ግረ ሰዶም ጉዳት በሚገባ ነግሮታል፡፡ በተለይ በዚህ ክረምት የተለየ ነገር ለማድረግ እየሞከርኩ ነው፡፡ ትምህርት ቤቶቻችንን ግን ከትምህርት ጥራትና ከክፍያቸው ባለፈ ወላጆች መከታተል አለብን፤ ልጆቻችንም የተለየ ነገር ሲያዩ እንዲነግሩን ማሳሰብ ይገባል፡፡ ዘመኑ ወላጅነት ከባድ የሆነበት ጊዜ ነው፡፡ ›› አሉኝ፡፡
ወላጆች ሆይ
እስኪ በጉዳዩ ላይ እንምከርበት፡፡ ከልጆቻችንም ጋር እንነጋገር፤ መምህራን በተማሪዎች ላይ ይህንን ነገር ፈጽመዋል ተብለው የሚከሰሱበት ጊዜ ላይ ነንና ልጆቻችን እንዳይታለሉ እንንገራቸው፤ ከሃይማኖት፣ ከሥነ ምግባር፣ ከባህል፣ ከጤናና ከማኅበራዊ ኑሮ አንጻር የሚያስከትለውን ችግር እንንገራቸው፡፡ እኛም ስለዚህ ጉዳይ መረጃ እንዲኖረን እንጠይቅ፣ እናንብብ፣ እንመካከር፤ ከተለያዩ አካባቢዎች ከምሰማው አንጻር በተለይ በከተሞች ውስጥ ችግሩ ሳይታሰብ ሥር እየሰደደ ነው፡፡ ሰሞኑን የቀረበ አንድ ይፋ ያልሆነ ጥናት በአዲስ አበባ ከተማ መሰናዶ ትምህርት ቤቶች በሚማሩ 2000 ተማዎች ላይ በተደረገ ጥናት 48% ተማሪዎች የጌይና ሌዝቢያን ደጋፊ መሆናቸው ታውቋል፡፡ እኒህ እናት እንዳሉት በዚህ ዘመን ወላጅነት ፈተና ውስጥ ገብቷል፡፡ ኃላፊነቱ ሰፍቷል፡፡ መሰናክሉ በዝቷል፡፡ እስኪ የፈጣሪን ርዳታ እየጠየቅን ይህንን ነገር የሰሞኑ የቤተሰብ አጀንዳ እናድርገው፡፡
Short URL: http://www.zehabesha.com/amharic/?p=4975

No comments:

Post a Comment