Wednesday, July 10, 2013

የ35 ሀገራት አምባሳደሮች የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበርን ጠርተው አነጋገሩ

በዘሪሁን ሙሉጌታ
በኢትዮጵያ የሚገኙ የ35 ሀገራት አምባሳደሮች የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር የሆኑትን ኢንጂነር ይልቃል ጌትነትን ጠርተው አነጋገሩ። ትናንት በአሜሪካን ኤምባሲ በተካሄደው የአምባሳደሮቹ ስብሰባ ላይ በቅርቡ የተመሰረተውንና በአዲስ አበባ ከተማ በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች የተገኙበትን ሰላማዊ ሰልፍ ማካሄድ የቻለውን ሰማያዊ ፓርቲ ብቻ ጠርተው አነጋግረዋል። በተለምዶ ‘‘የኢትዮጵያ ለጋሾች ቡድን’’ የሚል መጠሪያ ያለውና የአሜሪካንን ጨምሮ በርካታ የአውሮፓ ሀገራት አምባሳደሮች በአባልነት የሚገኙበት የለጋሾች ቡድን በተለያዩ ጊዜያት በሀገሪቱ የሚንቀሳቀሱ ከፍተኛ የተቃዋሚ አመራሮች ጋር በሀገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች ላይ እንደሚወያይ ይታወቃል። የአምባሳደሮቹ ቡድን ትናንት በአሜሪካ ኤምባሲ ባካሄደው ስብሰባ ላይ ሰማያዊ ፓርቲ በተለየ ሁኔታ ተጋብዟል። የፓርቲው ሊቀመንበርም ከአምባሳደሮቹ ጋር አንድ ሰዓት ተኩል የፈጀ ውይይት ማድረጋቸውን በተለይ ለሰንደቅ ጋዜጣ ገልፀዋል። ከአምባሳደሮቹ ጋር በተደረገው ውይይት ላይ የፓርቲው ፖሊሲ ምንነት፣ ፓርቲው በወጣቶች ላይ ከማተኮሩ አንፃር በስራ ዕድል ፈጠራ ላይ ምን አይነት ፕሮግራም እንዳለው፣ የኢኮኖሚ ፖሊሲው ምን እንደሆነ፣ የፌዴራሊዝምና የመሬት ፖሊሲው ምን እንደሚመስል፣ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሰሜን አፍሪካና የአረብ ሀገራት አይነት አብዮት ይነሳ ይሆን የሚለው ጨምሮ ሌሎች ፓርቲውን በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ውይይት መደረጉን ኢንጂነር ይልቃል ተናግረዋል። በተጨማሪም የፓርቲው ሊቀመንበር የፓርቲውን ራዕይ የሚያመለክት 10 ገፅ ያለው ፅሁፍ ለአምባሳደሮቹ እንዲደርሳቸው ማድረጉንም ገልፀዋል። ፓርቲው በአምባሳደሮቹ ቡድን ስብሰባ ላይ እንዲገኝ ከአንድ ወር በፊት ጥሪ እንደተደረገለት የጠቀሱት ኢንጂነር ይልቃል፤ 70 ከመቶ የኢትዮጵያ ወጣት ዕድሜው ከ35 በታች እንደመሆኑ፣ ፓርቲው ለወጣቶች የተለየ ትኩረት እንደመስጠቱ፣ የዲፕሎማሲ እውቅና መሰጠቱ ተገቢ መሆኑን የፓርቲው ሊቀመንበር አያይዘው ገልፀዋል። ፓርቲው ከተመሰረተ ጀምሮ በተናጠል ከኤምባሲዎቹ ጋር ሲሰራ መቆየቱን ያስታወሱት ኢንጂነር ይልቃል፤ ነገር ግን በለጋሾች ቡድን አመታዊ ስብሰባ ላይ በይፋ ንግግር እንዲያደርጉ መጋበዛቸው ለፓርቲው ከፍተኛ የፖለቲካ ጥቅም እንዳለውም ገልፀዋል። በተያያዘ ሰማያዊ ፓርቲ በየሳምንቱ ቅዳሜ በሀገሪቱ ፖለቲካ ላይ የወጣቶች ክርክር መድረክ ማዘጋጀት መጀመሩንና ባለፈው ቅዳሜና እሁድ በአዲስ ቪው ሆቴል ከፓርቲ አደረጃጀት ጋር በተያያዘ በፓርቲው የአደረጃጀት ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ 35 ለሚሆኑ የአሰልጣኞች ስልጠና መሰጠቱን የፓርቲው የሕዝብ ግንኙነት አስታውቋል። የአሰልጣኞች ስልጠናው ፓርቲው በቅርቡ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶችን ለመክፈት የቅድመ ዝግጅት ስራ አካል መሆኑንም የፓርቲው የሕዝብ ግንኙነት በላከው መግለጫ አስታውቋል።
(ምንጭ ሰንደቅ ጋዜጣ አዲስ አበባ ጁላይ 10 2013)
Short URL: http://www.zehabesha.com/amharic/?p=5130

No comments:

Post a Comment