Wednesday, December 20, 2017

የኦሕዴድና ብአዴን የፓርላማ አባላት ስብሰባ አንሳተፍም አሉ


(ኢሳት ዲሲ--ታህሳስ 11/2010) በኢትዮጵያ ፓርላማ የኦሕዴድና ብአዴን አባላት ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ በምክር ቤት ተገኝተው በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ ካልሰጧቸው በመደበኛ ስብሰባዎች አንሳተፍም አሉ።
የኦሕዴድና የብአዴን የሕዝብ ተወካዮች ምክርቤት አባላት ሀገሪቱን ስጋት ላይ በጣላት ብሄር ተኮር ግጭትና የፖለቲካ ቀውስ ላይ አቶ ሃይለማርያም ማብራሪያ እንዲሰጡ ጥያቄ አቅርበዋል።
አባላቱ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሱት በተወከሉባቸው የፖለቲካ ድርጅቶች ውይይት ካካሄዱ በኋላ ነው።
በኢትዮጵያ ያለው ቀውስ ከፖለቲካ ፓርቲ ሽኩቻ ወደ ፓርላማ አባላትም ተሸጋግሯል።
የወቅቱ የኢትዮጵያ ሁኔታ ያሳሰባቸው የኦሕዴድና የብአዴን ተወካይ የሆኑ የምክር ቤት አባላት በመደበኛ ስብሰባ ማሳተፍ ማቆማቸውን ነው የገለጹት።
ምክንያታቸው ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ሃገሪቱን ስጋት ላይ በጣለው ብሔር ተኮር ግጭትና የፖለቲካ ቀውስ ላይ መጀመሪያ ማብራሪያ ይስጡን በሚል ነው።
እናም የምክር ቤቱ አባላት ያቀረቡት ጥያቄ ምላሽ አግኝቶ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፓርላማ እስኪገኙ ድረስ መደበኛ ስብሰባዎችን አንሳተፍም ብለዋል።--የኦሕዴድና የብአዴን ተወካይ የፓርላማ አባላት።
አባላቱ ላቀረቡት ጥያቄ ከምክትል አፈ ጉባኤዋ ወይዘሮ ሽታዬ ምናለ ምላሽ እየተጠበቀ መሆኑን ሪፖርተር ጋዜጣ በዘገባው አመልክቷል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞም ባለፈው ሳምንት ሀሙስና ትላንት ማክሰኞ መካሄድ የነበረበት የፓርላማው መደበኛ ስብሰባ አለመካሄዱ ነው የተነገረው።
በምክር ቤቱ የአሰራርና የአባልነት ስነምግባር ደንብ መሰረት የፓርላማ አባላት ጠቅላይ ሚኒስትሩን በወር አንድ ጊዜ ጠርተው ማብራሪያ መጠየቅ ይችላሉ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ደንብ መሰረት በአመት 2 ጊዜ ዝርዝር የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ የማቅረብም ግዴታ አለባቸው።
በፓርላማ አባላቱ ጥያቄ መሰረት አፈ ጉባኤዋ ወይዘሮ ሽታዬ ምናለ ምላሽ ባይሰጡ ስለሚከተለው ሁኔታ በሕጉ የተቀመጠ ነገር የለም።
ጉዳዩን በተመለከተ ከሪፖርተር ጥያቄ የቀረበለት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል።

ምንጭ ኢሳት ዜና 

Sunday, August 27, 2017

በሳዑዲ አረቢያ ያሉ ኢትዮጵያውያን በግዳጅ እንዳይባረሩ ጥሪ ቀረበ

BBN news August 26, 2017
በሳዑዲ አረቢያ ያለ መኖሪያ ፈቃድ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ከሀገሪቱ እንዳይባረሩ ጥሪ ቀረበ፡፡ የሳዑዲ አረቢያ መንግስት ስደተኞቹን ለማባረር መግለጫ ማውጣቱን ተከትሎ ድምጹን ያሰማው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች፣ መንግስት በስደተኞቹ ላይ የማባረር እርምጃ እንዳይወስድ ጠይቋል፡፡ የሳዑዲ አረቢያ መንግስት በሀገሪቱ ያለ ህጋዊ ወረቀት የሚኖሩ ስደተኞች እንዲወጡ የሶስት፣ ቀጥሎም ሁለት ጊዜ የአንድ ወር ቀነ ገደብ መስጠቱ ይታወሳል፡፡ መንግስት ከትላንት በስቲያ እንዳስታወቀው፣ ስደተኞችን በኃይል የማስወጣት እርምጃ ሊወሰድ ነው፡፡
የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች፣ ሳዑዲ ይፋ ያደረገችውን ቀጣይ እርምጃ የምትፈጽም ከሆነ፣ ከግማሽ ሚሊዬን በላይ ወረቀት የሌላቸው ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የእርምጃው ሰለባ ይሆናሉ፡፡ በኃይል ሊወሰድ የሚችለውን እርምጃ ተከትሎ በርካቶች ሊጎዱ እንደሚችሉ ያስገነዘበው የሰብዓዊ መብት ተሟጋጅ ድርጅቱ፣ በተለይ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የፖለቲካ ጠብ ያላቸው ስደተኞች ይበልጥ ተጎጂ ሊሆኑ እንደሚችሉም አስጠንቅቋል፡፡ በሳዑዲ አረቢያ የኢኮኖሚ ስደተኞች የመኖራቸውን ያህል የኢትዮጵያ መንግስትን ሽሽት ወደ ሳዑዲ የተሻገሩ መኖራቸውን ያወሳው ድርጅቱ፣ ሳዑዲ ያለችውን እርምጃ የምትወስድ ከሆነ፣ የእነዚህ ስደተኞች ዕጣ ፈንታ የከፋ ሊሆን እንደሚችል ገልጿል፡፡
ስደተኞቹ በኃይል ተገድደው ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ የሚደረግ ከሆነ፣ በኢትዮጵያ ለህይወታቸው አስጊ የሆነ ነገር እንደሚጠብቃቸው የገለጸው የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ፣ ምናልባትም የኢትዮጵያ መንግስት ግድያን ጨምሮ መሰል እርምጃዎችን ሊወስድባቸው እንደሚችል ከወዲሁ ስጋቱን ገልጿል፡፡ ከዚህ ቀደም ከሳዑዲ አረቢያ በኃይል ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ ከተደረጉ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች መካከል በመንግስት ግድያ የተፈጸመባቸው መኖራቸውንም ሂውማን ራይትስ ዎች በመግለጫው አትቷል፡፡ ስለ ስደተኞች ብሎ የሳዑዲ አረቢያን መንግስት የሚማጸነው የድርጅቱ መግለጫ፣ ከሳዑዲ ባለስልጣናት በኩል እስካሁን ምላሽ አላገኘም፡፡ ሳዑዲ ያወጣችውን የምህረት ቀነ ገደብ ተከትሎ፣ ከ50 ሺህ የማይበልጡ ወረቀት የሌላቸው ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው መግባታቸው በመንግስት በኩል ሲገለጽ ቆይቷል፡፡

source BBN news August 26,2017