Tuesday, October 15, 2013

በደብረ ማርቆስ ዩነቨርስቲ ተማሪዎችና በመንግስት መካከል ረብሻ ተነስቷል

(ዘ-ሐበሻ)  ጥቅምት 4 ቀን 2006 ዓ.ም. በደብረማርቆስ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎችና በመንግስት መካከል ውጥረት ነግሷል፡፡ የችግሩ ዋነኛ መንስኤም በግቢው በሚቀርብ ምግብ ዙሪያ እና መንግስት የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ኃይማኖታዊ ስርዓትን
የተላበሰ አለባበስ መልበስ የተከለከለ ነው በሚል በተለይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ኃይማኖት ተካታዮችና የእስልምና ኃይማኖት ተከታዮች ድርጊቱን በመቃወማቸው ረብሻ ተቀስቅሷል፡፡ በዚህም በተፈጠረ አለመግባባት የፌደራል ፖሊስ ተማሪዎችን እየደበደበ ከግቢ ያስወጣ ሲሆን፤በዚህም የቆሰሉ ተማሪዎች እንዳሉ እና በአሁን ሰዓትም የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑም ተጠቁሟል፡፡
በተለይ ትናንት ሰኞ ማታ ጥቅምት 4 ቀን 2006 ዓ.ም. በርካታ ተማሪዎች በፈደራል ፖሊስ እየታደኑ እየታሰሩ እንደሚገኙ የተጠቆመ ሲሆን በከተማው ያሉ ወላጆችም በጉዳዩ እጅግ በመቆጣታቸው በዚህ ምሽትም በርካታ ወላጆችም በተማሪዎቹ ላይ እየተወሰደ ባለው እርምጃ በመቃወም ከቤታቸው ውጭ ከፌደራል ፖሊስና ከአማራ ክልል ፖሊስና አስተዳደር ጋር መፋጠጣቸውም ተነግሯል፡፡ በተፈጠረው ችግርም እስካሁን ምን ያህል ተማሪ እንደተጎዳ በቁጥርና መጠን ለማወቅ አልተቻለም፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ የዩኒቨርስቲው አስተዳደርንና የአማራ ክልል አስተዳደርና ፖሊስን  ለማናገር ብንሞክርም ስልካቸው ዝግ ነው፡፡ የነበረው አለመግባባትም ይህ እስከተዘገበበት ድረስ በግቢው በደንብ አለመረጋጋት እንዳለም ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

No comments:

Post a Comment