Saturday, February 28, 2015

ኢህአዴግ 98ቢሊዮን ብር ነጠፈበት!!

“ታላቅ ሥራ ተሰርቷል! እናመሰግናለን!” ኦባንግ
ኢህአዴግ በዓለም ባንክ በኩል ከእንግሊዝ የዓለምአቀፍ ልማት ተራድዖ መ/ቤት ሊለግስለት ታቅዶ የነበረው 4.9 ቢሊዮን ዶላር (98ቢሊዮን ብር) የገንዘብ ድጋፍ ነጠፈበት፡፡ አቶ ሬድዋን አልነጠፈብንም ይላሉ፡፡ ኦባንግ ሜቶ በበኩላቸው “የታላቅ ሥራ ውጤት ነው፤ እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ ጥቅምት 2፤2005 (October 12, 2012) “ኢህአዴግ በ600 ሚሊዮን ዶላር አጣብቂኝ ውስጥ ገባ!! ብያኔው ከጸና ኪሣራው በቢሊዮን ዶላር ሊደርስም ይችላል!” በሚል ርዕስ የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ያካሂድ ስለነበረው ፕሮግራም በዘገበበት ወቅት የሚከተለውን ዜና አትሞ ነበር፡- “ከ1998ዓም ጀምሮ የመሠረታዊ አገልግሎት ጥበቃ ፕሮግራም (Protection of Basic Services “PBS Program”) በሚል በአራት ተከታታይና ሁለት ተጨማሪ የገንዘብ ድጎማ የሚደረግባቸውን ፕሮግራሞች የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ሲያካሂድ ቆይቷል፡፡ ይህ መሠረታዊ የሆኑ አገልግሎቶችን ለማሟላት ተወጥኖ የሚካሄድ ፕሮጀክት በትምህርት፣ በጤና፣ በእርሻ፣ በንጹህ ውሃ አቅርቦት፣ በገጠር መንገድ ሥራ፣ ወዘተ መስኮች ላይ እንዲውል (PBS I, PBS I-AF (Additional Financing), PBS II, PBS 11-AF, PBS-Social Accountability Program and PBS III) በማለት በተለያዩ ደረጃዎች ለተከፋፈለው ኦፐሬሽን ማስፈጸሚያ የሚውለው ገንዘብ ከ13ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ ከፍተኛው የዓለም ባንክ ድርሻ 2ቢሊዮን ዶላር ሲሆን የተቀረው በሌሎች ለጋሽ መንግሥታት እና ድርጅቶች የሚሸፈን ነው፡፡ PBS III የተሰኘውን በሦስት ንዑሳን ፕሮግራሞች የተከፋፈለውን ፕሮጀክት ለማስፈጸም በአጠቃላይ የሚፈጀው 6.3ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው፡፡”
ይህ ለመሠረታዊ ልማት እንዲውል በዓለም ባንክ በኩል የሚሰጠውን ገንዘብ የሚደጉሙት ምዕራባውያን አገራት ሲሆኑ አንዷ ተጠቃሽ አገር እንግሊዝ ናት፡፡ ሆኖም ኢህአዴግ ከምዕራባውያን በዓለም ባንክ በኩል የሚያገኘውን ገንዘብ ለራሱ የፖለቲካ መጠቀሚያነት እያዋለው መሆኑ ለዓለም ባንክ ተደጋጋሚ መረጃዎች ሲቀርቡ ቆይተዋል፡፡ በተለይ ሟቹ መለስ በቀጥታ በሰጡት ትዕዛዝ 424 የአኙዋክ ተወላጆች ከተገደሉ በኋላ ኢህአዴግ በቦታው ያሰማራው የመከላከያ ሠራዊት በሥፍራው የሚኖሩትን ከመኖሪያ ቀያቸው በማፈናቀል እምቢ ያሉትን በግድ በማስነሳት፣ በመግደል፣ አስገድዶ በመድፈር፣ በማሰቃየት፣ ወዘተ ግፍ ሲፈጽም መቆየቱ በተለያዩ ዓለምአቀፋዊ ዕውቅና ባገኙ ዘገባዎች ሲነገር ቆይቷል፡፡ የዓለም ባንክ ለመሠረታዊ ልማት በማለት የሚሰጠው ገንዘብ ኢህአዴግ ወታደሮቹን የግፍ ሥራ ላይ በማሰማራት ደመወዝ የሚከፍልበት መሆኑን በመጥቀስ ወደ ኬኒያ የተሰደዱ የክልሉ ነዋሪዎች አቤቱታ አቅርበው እንደነበር ጎልጉል በወቅቱ የዘገበው ዜና ነበር፡፡ ““ኢህአዴግ አንገቱን ታንቋል”፤ዓለም ባንክ ርምጃ ለመውሰድ ጫፍ ደርሷል” በሚል ርዕስ የተጻፈውን ዜና ለማንበት እዚህ ላይ ይጫኑ፡፡
money lostከዚሁ ጋር በተያያዘ “ሚስተር ኦ” በመባል የሚጠሩት አኙዋክ ተወላጅ ኢህአዴግ የዕርዳታ ገንዘብ ለሰብዓዊ መብት ረገጣና ለራሱ የፖለቲካ መጠቀሚያነት እንዳዋለው በመጥቀስ የእንግሊዝ መንግሥት ከግብር ከፋይ ዜጎቹ የሚያገኘውን ገንዘብ አምባገነንነት እየደገፈበት መሆኑን በተለይም የዓለምአቀፍ ልማት ተራድዖ መ/ቤቱ ተጠያቂ ስለሆነ ከዚህ እንዲታቀብ ክስ መመሥረታቸው ይታወቃል፡፡ የክሱ ሒደት እየተካሄደ ባለበት ባሁኑ ወቅት ሚስተር ኦ በተደጋሚ እንደመሰከሩት ኢህአዴግ ነዋሪዎችን በግዳጅ ከቀያቸው በማፈናቀል የሚያካሂደው የግዳጅ ሰፈራና የመንደር ምሥረታ ሕገወጥ መሆኑ በመቃወማቸው በተደጋጋሚ ከፍተኛ ድብደባ እንደረሰባቸው ተናግረዋል፡፡ ብዙዎች ለአካላዊ ሥቃይ ደርሶባቸዋል፣ ሴቶች ክብረንጽህናቸው ተደፍሯል፣ አዛውንትና ህጻናት ለአሰቃቂ መከራ ተዳርገዋል፤ ይህንንም እርሳቸው እንዳዩ ሚስተር ኦ ይመሰክራሉ፡፡
የሚስተር ኦ የፍርድቤት ጉዳይ ወደ ውሳኔ ሊደርስ ባለበት ወቅት የልማት መ/ቤቱ ይህንን ዓይነት ውሳኔ መውሰዱ ከፍርድ ቤቱ ጉዳይ ጋር የሚያያዝ እንደሆነ ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ ይናገራሉ፡፡ የልማት ተራድዖ መ/ቤቱ ቃል አቀባይ ግን የመ/ቤታቸው ውሳኔ ከሚስተር ኦ የፍርድቤት ጉዳይ ጋር ያልተያያዘ እንደሆነ መናገራቸውን የእንግሊዙ ዘጋርዲያን ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ መ/ቤቱ ለዚህ ውሳኔ የደረሰው ኢትዮጵያ “የዕድገት ስኬት” እያስመዘገበች በመምጣቷ የመሠረታዊ ልማት አገልግሎት የገንዘብ ዕርዳታ የማያስፈልጋት በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡
ይህ መጠኑ እጅግ ከፍተኛ የተባለውና ለኢህአዴግ ንጹህ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ የሚያስገኝ ገንዘብ እንደነጠፈበት መሰማቱን አስመልክቶ ጋዜጣው የኢህአዴግ ፅ/ቤት ሃላፊ የሆኑትን ሬድዋን ሁሴን በጠየቃቸው ወቅት የመለሱት አልነጠፈብንም የሚል እንድምታ ያለው ነው፡፡ “እነርሱ ያሉት ዕርዳታውን አንሰጥም ወይም እናቆማለን ሳይሆን ዕርዳታ አሰጣጡ እንደገና ይዋቀራል ነው” በማለት ሬድዋን ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ ሆኖም 4.9 ቢሊዮን ዶላር (98ቢሊዮን ብር) ዕርዳታ ለመስጠት ከዓለምባንክ ጋር ስምምነት የነበረው የእንግሊዝ የልማት ተራድዖ መ/ቤት “ኢትዮጵያ አድጋለች” በማለት በ2015/2016 በፓውንድ 256ሚሊዮን ብቻ (5በመቶ) ዕርዳታ ለመስጠት መወሰኑን የኢህአዴግ ጽ/ቤት ሃላፊው ሬድዋን ሁሴን አላብራሩም፡፡
ኢህአዴግ ለዕርዳታ የሚሰጠውን ገንዘብ ዜጎችን ለማሰቃየት፣ ወታደር ለመቀለብ፣ ወዘተ እንደሚጠቀምበት በተደጋጋሚ ዘገባዎች እና ማስረጃዎች ሲወጡበት የከረመ ቢሆንም ማስረጃዎቹን ተከትሎ የዓለም ባንክ በዕርዳታ አሠጣጡ ላይ አንዳች ውሳኔ እንዳያደርግ ብዙ ሲደክም ቆይቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ጉዳዩ ውሳኔ ሳይሰጥበት እንዲስተጓጎል በማድረግ ለሁለት ዓመታት ያህል እንዲጓተት ማድረጉን ከጉዳዩ ጋር ቅርበት ያላቸው ወገኖች ይመሰክራሉ፡፡
ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ (አኢጋን) ዋና ዳይሬክተር የሆኑት ኦባንግ ሜቶ ጉዳዩን ገና ከጅምሩ የሚያውቁትና ድርጅታቸው ለዓመታት ሲሰራበት የነበረ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በመሆኑንም ይህንን የእንግሊዝ የልማት ተራድዖ መ/ቤት ውሳኔ የጋራ ንቅናቄያቸው ከደጋፊዎቹ ጋር በመሆን ያገኘው ድል እንደሆነ በፌስቡክ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት አስታውቀዋል፡፡ “ገና ከጅምሩ ከጋራ ንቅናቄያችን ጋር በመሆን ይህንን ሥራ በመደገፍ የተባበራችሁንን ሁሉ እንኳን ደስ አላችሁ ለማለት እወዳለሁ፤ ታላቅ ሥራ ተሰርቷል፤ እናመሰግናለን” ብለዋል “ጥቁሩ ሰው” ኦባንግ ሜቶ፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ አቶ ኦባንግ በተለይ ከጎልጉል ለቀረበላቸው አጭር ጥያቄ በሰጡት አስተያየት የጋራ ንቅናቄያቸው ደስታውን የገለጸው የልማት ገንዘብ በመቋረጡ ሳይሆን በልማት ስም የሚሰጠው ዕርዳታ ለሰብዓዊ መብት ረገጣ በመዋሉና ለዚህም ደግሞ ከበቂ በላይ ማስረጃ ድርጅታቸው ያለው በመሆኑ ነው፡፡ “አገር ብትለማ የሁሉም ደስታ ነው” ያሉት ኦባንግ አገርን በማልማት ሽፋን ደጋፊና ተቆርቋሪ የሌላቸውን ንጹሃን መበደልና የመኖር መብታቸውን መንፈግ ግን በየትኛውም መልኩ እርሳቸውም ሆነ አኢጋን የሚቀበለው እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡
ኢህአዴግ በቅርቡ አካሂዳለው ለሚለው ምርጫ እንደ ዕቁብ ዕጣ በማውጣትና በማስወጣት “አልደረሳችሁም” እያለ የተቀናቃኝ ፓርቲ አመራሮችን ከምርጫ እያስወገደ ባለበት፤ ሌሎችንም ሕጋዊ አይደላችሁም እያለ በተለጣፊ ድርጅት በማስበት ኅልውናቸውን እያሳጣ ባለበት ባሁኑ ወቅት በዜጎቹ ላይ የሚያካሂደውን መረን የለቀቀ የመብት ገፈፋ ለሥልጣን ያበቁትን ምዕራባውያንን ያስደሰተ እንዳልሆነ ይነገራል፡፡ የአውሮጳ ኅብረት ምርጫውን አልታዘብም ከማለቱ በተጨማሪ በሚዲያ ላይ የተጫነው አፈና በዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ድርጅት ይፋ ከሆነ ወዲህ ማነቆው በኢህአዴግ ላይ እየከረረ መምጣቱን ያሳያል፡፡ ኢህአዴግን ለሥልጣን ከማብቃት አልፋ ነፍጥ አንጋቢዎቹን የህወሃት መሪዎች ጸጉርና ጺም ከርክማ፤ ልብስ አልብሳ፤ ቋንቋ አስተምራ፤ የከተማ አኗኗር እንዴት እንደሆነ አሠልጥና፣ ቶሎ ባይገባቸውም ፕሮቶኮል አስተምራ፣ እስካሁንም ተንከባክባ እዚህ ድረስ ያቆየቻቸው እንግሊዝ እንዲህ ያለውን የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ስታደርቅ “ቀጣዩስ ምን ይሆን?” የሚል ጥያቄ እንዲነሳ አድርጓል፡፡ “ምዕራባውያን መግደልም ማንሳትም ያውቁበታል” በማለት አስተያየት የሚሰጡ ወገኖች እንደሚሉት ቀጣዩ የኢህአዴግ ጉዞ በከፍተኛ ሁኔታ ለህወሃት ሲቀጥል ለኢህአዴግ አስጊ ከመሆን ባሻገር በውጭ ምንዛሪ እጥረት በየጊዜው የሚፈጠረውን ግሽበት በዕርዳታ ገንዘብ የሚያስተካክለው ኢህአዴግ እንዲህ ያለው የገንዘብ ማዕቀብ ክፉኛ ያነጥፈዋል ሲሉ ግምታቸውን ይሰጣሉ፡፡ ሙስናው መረን በለቀቀባት አገር ከሕዝብ እየተዘረፈ በተለያዩ አገራት ባንኮች በውጭ ምንዛሪ የሚከማቸውን ገንዘብ በሚካፈሉትም ላይ የድርሻ ቅነሳ የማስከተሉ ጉዳይ አብሮ የሚታይ እንደሆነ ይነገራል፡፡
ከዚህ ዜና ጋር ተያያዥነት ያለውን ጥቅምት 2፤2005 (October 12, 2012) ያተምነውን ዜና ከዚህ በታች እንደሚከተለው እንደገና አትመነዋል፡፡

ኢህአዴግ በ600 ሚሊዮን ዶላር አጣብቂኝ ውስጥ ገባ!!

ብያኔው ከጸና ኪሣራው በቢሊዮን ዶላር ሊደርስም ይችላል!

ኢህአዴግ ከዓለም ባንክ ያገኘውን 600 ሚሊዮን ዶላርና በተመሳሳይ ፕሮጀክት ወደፊት ሊያገኝ የሚችለውን ከፍተኛ ገንዘብ በተመለከተ አደጋ ውስጥ መውደቁ ተሰማ። ኢንስፔክሽን ፓናል (Inspection Panel – IP) የተሰኘ ተቋም ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያመለክተው ኢህአዴግ የቀረበበት ውንጀላ ከተረጋገጠ የሚያጣው ገንዘብ በቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ ታውቋል። ይፋ የሆነውን መረጃ አስመልክቶ ከኢህአዴግ ወገን እስካሁን በይፋ የተሰጠ ምላሽ የለም።
ግፍ የሚፈጽሙ መንግስታትን፣ በልማት ስም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚፈጽሙ ወንጀሎችን መረጃዎችን በስፍራው በመገኘትና ከመሠረቱ ዘልቆ በመግባት አደራጅቶ ተጠያቂ የሚያደርገው ኢንክሉሲቭ ዴቨሎፕመንት ኢንተርናሽናል Inclusive Development International (IDI) ከሰለባዎቹ ውክልና ተሰጥቶታል። ተቋሙም በውክልናው መሰረት ለኢንስፔክሽን ፓናል በዝርዝር የሰለባዎቹን በደል በማተት አሳውቋል።
የኢህአዴግ መከላከያ ሠራዊት የሚያደርሰውን እስራት፣ ግርፋት፣ አስገድዶ መድፈር፣ ከመኖሪያ ቦታ ማፈናቀል፣ የግዳጅ ሰፈራ ወዘተ በማምለጥ ወደ ኬንያ የተሰደዱ የጋምቤላ ነዋሪዎች ይህ ሁሉ ግፍ የሚፈጽምባቸው የኢትዮጵያ መንግሥት በልማት ስም ከዓለም ባንክ በሚያገኘው የዕርዳታ ገንዘብ በመሆኑ ለባንኩ በላኩት የአቤቱታ ደብዳቤ አመልክተዋል።
አቤቱታውን መሠረት በማድረግ የሚደረገው ምርመራ ውጤት ይፋ ሲሆን፣ በሌሎች አገሮች እንደተደረገው በዕርዳታ ስም የሚገኝን ገንዘብ ኢህአዴግ ለፖለቲካ ተግባር መጠቀሙ ሲረጋገጥ፣ በመስከረም ወር መጀመሪያ አካባቢ ከዓለም ባንክ ተፈቅዶ የነበረው 600ሚሊዮን ዶላር ሊከለከል ይችላል፡፡
የዛሬ ዘጠኝ ዓመት አካባቢ በሟቹ ጠ/ሚ/ርና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዝ በጋምቤላ ክልል በተለይ የተማሩ ወንዶች ላይ በማተኮር 424 ንጹሐን የአኙዋክ ተወላጆች በተገደሉበት ወቅት በሺዎች የሚቆጠሩት ወደ ጎረቤት አገር ኬንያ መሰደዳቸው ይታወሳል፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ክልሉ ሰላም የለም፡፡ በየጊዜውም የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ሲካሄዱበት ቆይቷል፡፡ በተለይም ለም የሆነውን እጅግ ሰፋፊ መሬት ለውጪ ባለሃብቶች በሳንቲም በመሸጥ ላይ የሚገኘው የኢህአዴግ አገዛዝ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በቀድሞው የደርግ ዘመን ሲካሄድ ከነበረው ባለፈ መልኩ እጅግ በሚያሰቅቅ ሁኔታ በመንደር ምስረታና አስገድዶ የማስፈር ፖሊሲ ከመኖሪያ ቀዬ የማፈናቀል ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን የኦክላንድ ተቋም፣ ሂውማን ራይትስ ዎች፣ … የመሳሰሉ ድርጅቶች ያወጧቸው ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡
ከ1998ዓም ጀምሮ የመሠረታዊ አገልግሎት ጥበቃ ፕሮግራም (Protection of Basic Services “PBS Program”) በሚል በአራት ተከታታይና ሁለት ተጨማሪ የገንዘብ ድጎማ የሚደረግባቸውን ፕሮግራሞች የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ሲያካሂድ ቆይቷል፡፡ ይህ መሠረታዊ የሆኑ አገልግሎቶችን ለማሟላት ተወጥኖ የሚካሄድ ፕሮጀክት በትምህርት፣ በጤና፣ በእርሻ፣ በንጹህ ውሃ አቅርቦት፣ በገጠር መንገድ ሥራ፣ ወዘተ መስኮች ላይ እንዲውል (PBS I, PBS I-AF (Additional Financing), PBS II, PBS 11-AF, PBS-Social Accountability Program and PBS III) በማለት በተለያዩ ደረጃዎች ለተከፋፈለው ኦፐሬሽን ማስፈጸሚያ የሚውለው ገንዘብ ከ13ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ ከፍተኛው የዓለም ባንክ ድርሻ 2ቢሊዮን ዶላር ሲሆን የተቀረው በሌሎች ለጋሽ መንግሥታት እና ድርጅቶች የሚሸፈን ነው፡፡ PBS III የተሰኘውን በሦስት ንዑሳን ፕሮግራሞች የተከፋፈለውን ፕሮጀክት ለማስፈጸም በአጠቃላይ የሚፈጀው 6.3ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ የባንኩ ድርሻ የሆነውን 600ሚሊዮን ዶላር ቦርዱ መስከረም 5ቀን 2005ዓም አጽድቋል፡፡
በአስገድዶ ማስፈር፣ መንደር ምስረታና ሌሎች በርካታ የሰብዓዊ መብቶቻቸው የተጣሱባቸው በኬንያ የሚገኙ ሦስት የአኙዋክ ስደተኞች ተወካይ ድርጅቶች በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙ ሌሎች የሰብዓዊ ድርጅቶች ጋር በመሆን ባንኩ ሊሰጥ የወሰነውን ገንዘብ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቅም ከመዋል ይልቅ ለኢህአዴግ የፖለቲካ ዓላማ ማስፈጸሚያ እየዋለ መሆኑን በመጥቀስ ለባንኩ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጂም ዮንግ ኪም መስከረም 6፤ 2005ዓም ደብዳቤ ልከዋል፡፡ በጥያቄያቸውም መሠረት በዓለም ባንክ በኩል ወደ ኢትዮጵያ የሚፈሰው ገንዘብ “በልማት ስም የኢትዮጵያ መንግሥት በጋምቤላ ክልል ለሚያካሂደው የመንደር ምስረታ እየዋለ ነው” በማለት ይከሳል፡፡ ሲቀጥልም የአኙዋክ ሕዝብ ለዘመናት ከኖረበት መንደር በማፈናቀል “የተሻለ አገልግሎት ይሰጣችኋል” በማለት በግድ የማስፈር ተግባር እየተፈጸመ ሲሆን “የተባለው አገልግሎትም ሆነ ለእርሻ የሚሆን በቂ ቦታ እንዲሁም ለከብቶች የሚበቃ የግጦሽና የውሃ ቦታ የላቸውም” በማለት ሰፈራውን የተቃወሙ ሁሉ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብት ረገጣ እየደረሰባቸው እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡ ይህንን ግፍ የሚፈጽሙት ደግሞ የዓለም ባንክ ለመሠረታዊ አገልግሎት ጥበቃ ፕሮግራም (Protection of Basic Services “PBS Program”) ስም ለልማት እንዲውል ከሚሰጠው የዕርዳታ ገንዘብ በመንግሥት ተቀጥረው ደመወዝ የሚከፈላቸው ሠራተኞች መሆናቸውን ገልጾዋል፡፡ ይህንን ጉዳይ ከዓለም ባንክ ጋር እንዲነጋገሩላቸው Inclusive Development International (IDI) የተባለውን ድርጅት መወከላቸውን አስታውቀዋል፡፡ (የደብዳቤው ሙሉ ቃል እዚህ ላይ ይገኛል)
ተመሳሳይ ጉዳዮችን በዓለምአቀፍ ደረጃ በመከታተልና በማስፈጸም የታወቀው IDI በመስከረም ወር አጋማሽ ላይ ጉዳዩ በቀጥታ ለሚመለከተው የመልሶ ማቋቋምና ልማት ዓለምአቀፍ ባንክና (International Bank for Reconstruction and Development (IBRD)) የዓለምአቀፍ ልማት ማኅበር (International Development Association (IDA)) ሥር ለሚገኘው የኢንስፔክተር ፓናል ባለ 18ገጽ ደብዳቤ ጽፏል፡፡ (የደብዳቤው ሙሉ ቃል እዚህ ላይ ይገኛል) ይህ የኢንስፔክተር ቡድን ከፍተኛ ሥልጣን ያለው መ/ቤት ሲሆን የዓለም ባንክ የሚሰጠውን ገንዘብ በትክክለኛ ቦታ ላይ አለመዋሉን በመጥቀስ ክስ የሚያቀርቡ ወገኖችን ጉዳይ በመከታተልና ቦታው ድረስ የራሱን ምርመራ በማካሄድ ውጤቱ ተግባራዊ እንዲሆን የባንኩን እጅ የማስጠምዘዝ ዓቅም ያለው እንደሆነ ከዚህ በፊት ያካሄዳቸው የምርመራ ውጤቶች ይጠቁማሉ፡፡
ይህ የመርማሪ ቡድን የቀረበለትን አቤቱታ መቀበሉንና በጉዳዩ ላይ የማንም ተጽዕኖ የማይደረግበትን የራሱን ምርመራ እንደሚያደርግ ከትላንት በስቲያ ባወጣው ባለ 8ገጽ መግለጫ ላይ አሳውቋል፡፡ ይህ የአቤቱታ ፋይል ቁጥር የተሰጠው ጉዳይ በግልባጭ ለባንኩ ፕሬዚዳንትና ለከሳሽ ተወካይ ድርጅት (IDI) እንዲደርስ ተደርጓል፡፡(የደብዳቤው ሙሉ ቃል እዚህ ላይ ይገኛል)
ጎልጉል የሰሜን አሜሪካ ዘጋቢ ባጠናከረው መረጃ መሠረት ቡድኑ ከያዝነው ዓመት የጥቅምት አጋማሽ በኋላ ወደ ምስራቅ አፍሪካ ያቀናል። ቡድኑ ስደተኞቹ የሚገኙባቸውን፣ እንዲሁም ጉዳዩን በሚመለከት አስፈላጊ የሚላቸውን ቦታዎችና ግለሰቦች ሙሉ በሙሉ ያነጋግራል። ለስራው መሳካት የሚሆነውን ሁሉ በሚፈለግበት ቦታ በመገኘት በግንባር እንደሚያከናውን ለማወቅ ተችሏል።
በተለያየ ጊዜ ኢህአዴግ የሚፈጽመውን ግፍና በደል በማደራጀት ሥርዓቱ ላይ ከትጥቅ የጠነከረ ትግል ማካሄድ እንደሚቻል አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል:: አያይዘውም በመላው አገሪቱ የሚፈጸመውን የሰብአዊ መብት ረገጣና የመብት ጥሰት በማሰባሰብ የኢህአዴግን የገንዘብ ምንጭ የማድረቅ፣ ብሎም በእርዳታ ገንዘብ የሚገነባቸውን የአፈና ተቋማት ማስለል እንደሚቻል አስታውቀዋል። ይህንን ታላቅ ስራ የሰሩትን አካላት ልምዳቸውን ለሌሎች በማካፈል አስፈላጊውን ስራ ሊሰሩ እንደሚገባም አሳስበዋል። (የመግቢያው ፎቶ የተወሰደው: ዘጋርዲያን)
ምንጭ www.goolgule.com

Friday, February 27, 2015

ምርጫ ለኢትዮጵያ ወታደርና ፓሊስ: – ለህወሓት ባርነት ወይስ ለኢትዮጵያ ነፃነት

የኢትዮጵያ ሕዝብ ለውትድርና ከፍተኛ ክብር አለው። ውትድርና ከሙያና ሥራ በላይ የነፃነትና የክብር መገለጫ፤ ሀገርን ከባዕድ ወረራ መከላከያ ጋሻ ነው ብሎ ያምናል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ህግና ሥርዓት አክባሪ በመሆኑ ለፓሊስም ከፍተኛ አክብሮት አለው። የፓሊስ ሥራ ወንጀልን መከላከልና ወንጀለኞችን ወደ ፍርድ ማቅረብ መሆኑ በኢትዮጵያ ባህል የተከበረ ቦታና እውቅና አለው።
በህወሓት የአገዛዝ ዘመን ግን ይህ እየተቀየረ ነው። የህወሓት አዛዦች እየመሩት ያለው የኢትዮጵያ ጦር ሠራዊት ሀገርን ከባዕድ ጠላት ከመከላከል ጋር ምንም ዝምድና በሌላቸው ሁለት አበይት ተግባራት ላይ ተጠምዷል። በህወሓት አዛዦች የሚመራው ሠራዊት ዋነኛ ተግባር ለሰብዓዊ መብቶቻቸው መከበር እና ለፍትህ መስፈን የሚታገሉ ዜጎችን ማጥቃት ሆኗል። የጦሩ ሁለተኛው አቢይ ተግባር ደግሞ ለአዛዦች የግል ጥቅም ማካበቻ ገቢዎችን በሚያስገኙ ሥራ ላይ መሠማራት ነው።
የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት ኢትዮጵያዊያንን ማጥቂያ ሠራዊት መሆኑ ሲቪሉን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን የሠራዊቱንም አባላትን ጭምር ለህሊና ወቀሳ የዳረገ ጉዳይ ነው። ሆኖም ግን ይህ በህሊና ወቀሳ ብቻ ሊታለፍ የማይችል ወንጀል ነው። ሠራዊቱ በህወሓት እየታዘዘ የሚዘምተው በገዛ ራሱ ልጆች፣ እህቶች፣ ወንድሞችና ወላጆች፤ በገዛ ራሱ ጥቅሞች እና በገዛ ራሱ ላይ መሆኑ መገንዘብ ይኖርበታል። በገዛ ራሱ ጥቅሞች ላይ የሚዘምት አንድም ህሊና የሌለው አሊያም ነፃነት የተነፈገው ሰው ብቻ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ሠራዊቱ እየተራበና እየታረዘ አለቆቹ የታላላቅ ህንፃዎች ባለቤቶች፣ ባለፋብሪካዎች፣ የባንክና የኢንሹራንስ ኩባንያዎች ባለአክሲኖች የሚሆኑበት ሥርዓት ከዳር ሆኖ የሚመለከት መሆኑ የሚገርም ነው። ሠራዊቱ ቤተሰቦቹን መመገብ አቅቶት እያለ የአዛዦቹ ልጆች ለሽርሽር ዓለምን ይዞራሉ። እንዴት ነው ሠራዊቱ እየደኸየና እየሞተ አዛዦቹ እየከበሩ የሚሄዱት? ይህ አዋራጅ ሁኔታ እንዲያበቃ መታገል የሠራዊቱ ግንባር ቀደም ኃላፊነት ነው። ሠራዊቱ ወይ ባርነትን አሜን ብሎ መቀበል አለበት አለበዚያም እሱም እንደነሱ ሰው መሆኑን ማሳየት መቻል አለበት። በኢትዮጵያ ውስጥ የህወሓት አገዛዝ ወድቆ የሕዝብ ይሁንታ ያገኘ መንግሥት መመሥረቱ በከፍተኛ ሁኔታ ከሚጠቅማቸው የኅብረተብ ክፍሎች ግንባር ቀደሙ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ናቸው። በዚህም ምክንያት የሠራዊቱ አባላት ለሥርዓቱ መውደቅ በግልጽም በስውርም መታገል የዜግነት ብቻ ሳይሆን አዕምሮ ያለው ሰው ሆነው በመፈጠራቸው የተቀበሉት ግዴታ ነው።
ፓሊስን በተመለከተም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። ህወሓት የኢትዮጵያን ሕዝብ አፍኖ ለመግዛት የቻለው በዋኛነት የፓሊስን ኃይል ለአፈናው ተግባር የሚጠቀም በመሆኑ ነው። የተቃውሞ ድምጾች በተሰሙ ቁጥር የኢትዮጵያ ፓሊስ በወገኖቹ ላይ የሚያወርደው ዱላ የሚዘገንን ሆኗል። ሰላማዊ ሰልፈኞችን በጥይት መግደልና ማቁሰል፤ አረጋዊያንን፣ ሴቶችንና ሕፃናትን መግደል፣ ማቁሰል፣ መደብደብ በዚህ ተግባር የተሠማሩ ፓሊሶችን በቡድንም በግልም በህግ የሚያስጠይቅ ከባድ ወንጀል ነው። በህወሃት እየተመራ ያለው የኢትዮጵያ ፓሊስ ተግባራት ተበዳዮችን ብቻ ሳይሆን ራሱ ፓሊስንም ጭምር አንገት የሚያስደፋ ተግባር ነው። ለመሆኑ አንድ ተራ የኢትዮጵያ ፓሊስ ባልደረባ ከህወሓት አገዛዝ ምን ተጠቀመ? መልሱ “ምንም” የሚል ነው። ይልቁንስ በህወሓት የአገዛዝ ዘመን ፓሊስ የተናቀና የተዋረደ ሥራ ሆነ። በህወሓት አገዛዝ ፓሊስ እንደሰለጠነ አዳኝ ውሻ “ያዝ” ሲሉት የሚነክስ፣ የሚያደማ፣ የሚቦጭቅ ሆኗል። ይህ ለፓሊስ፣ ወንጀልም ውርደትም ነው። በህወሓት አገዛዝ መገርሰስ እና በምትኩ የህግ የበላይነት የሰፈነበት ሥርዓት መስፈን ፓሊስ ከሁሉ በላይ ተጠቃሚ ነው፤ ሰብዓዊ ክብሩን ያረጋግጥለታልና።
ዛሬ በኢትዮጵያችን ውስጥ የታዘዙትን የሚፈጽሙ የጦርና የፓሊስ ሠራዊት አባላት ስላሉ ነው የህወሓት ሹማምንት ልባቸው ያበጠው። ለማስረጃ ያህል ሰሞኑን የህወሓቱ ሹም አባይ ፀሐዬ የአዲስ አበባ ዙሪያ ገበሬዎች በግዴታ መነሳታቸው የሚቃወሙትን ዜጎችን ሁሉ ”ልክ እናስገባቸዋለን” ብሎ በሸንጎ የዛተው የታዘዘውን የሚፈጽም የጦርና የፓሊስ ሠራዊት መኖሩን ተማምኖ ነው። እስከ መቼ የኢትዮጵያ ጦር ሠራዊትና ፓሊስ ሕዝብን ማስፈራሪያ መሣሪያ ይሆናል?
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የኢትዮጵያ የመከላከያና የፓሊስ ሠራዊት አባላት ለራሳቸው እና ለወገናቸው የሚበጀው ሥርዓት የቱ እንደሆነ ያውቃሉ ብሎ ያምናል። በዚህም ምክንያት ስብዕናቸውን እያዋረደ እና እያደኸያቸው ያለውን የህወሓት አገዛዝን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር በመሆን ይፋለሙታል ብሎ ያምናል። ይህ ውሳኔ ግን ሠራዊቱ በጅምላ ሳይሆን እያንዳንዱ የሠራዊቱ አባል በግሉ የሚወስደው ውሳኔ እንደሆነ አርበኞች ግንቦት 7 ይገነዘባል።
በዚህም መሠረት ተደጋጋሚ ጥሪ እየተደረገለት፤ ጥሪውንም እየሰማ ከህወሓት ጋር ወግኖ ሕዝብን መውጋት የቀጠለ የሠራዊቱ አባል ላደረሰው ጥፋት በግል መጠየቁ የማይቀር መሆኑ ሊገነዘብ ይገባል። በእያንዳንዳንዱ የጦርና ፓሊስ ሠራዊት ባልደረባ ፊት የቀረበው ምርጫ “ለህወሓት ባርነት ታድራለህ ወይስ ራስህንና ሀገርን ነፃ ታወጣለህ” የሚል ነው።
ራስህንና ሀገርህን ነፃ ለማውጣት የመረጥክ የሠራዊቱና የፓሊስ ባልደረባ አሁኑኑ ሕዝባዊ ትግሉን ተቀላቀል። እስከዛሬ የበደልከውን ሕዝብ ለመካስ ምቹ ሁኔታ አለህ። በግልጽ የነፃነት ኃይሎችን እንድትቀላቀል፤ አሊያም አለህበት ሆነህ በውስጥ አርበኝነት እንድትደራጅና ተግባራዊ ሥራ እንድትጀምር መንገዱ ተመቻችቶልሃል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!
Source www.ginbot7.org

Monday, February 23, 2015

ድል የአላማ ጽናት እንጂ የመሳሪያ ጋጋታ ዉጤት አይደለም

ጣሊያን ዋና ከተማ ሮም ዉስጥ ዋና ከተማዋን ከተለያዩ የጣሊያን ከተሞችና ጣሊያንን ከፓሪስ፤ከሙኒክ፤ከጄኔቫና ከቪዬና ጋር የሚያገናዉና በአመት ከ 150 ሚሊዮን በላይ መንገደኞችን የሚያስተናግድ አንድ ትልቅ የባቡር መስመር አለ። ይህ የባቡር መስመር የሚጠራዉ ሮማ ተርሚኒ እየተባለ ሲሆን የባቡር መስመሩ አድራሻ ደግሞ የአምስት መቶዎቹ አደባባይ በመባል ይታወቃል። ወደዘህ ትልቅ ባቡር መስመር ሲገባ አንድ እጅግ በጣም ትልቅ ሀዉልት ወለል ብሎ ይታያል፤ ይህም ሀዉልት የአምስት መቶዎቹ አደባባይ ወይም ፒያዛ ዴ ቺንኮቼንቶ በመባል የታወቃል። የፒያሳ ዴ ቺንኮቼንቶ መታሰቢያ ሀዉልት የተሰራዉ ወራሪዉ የጣሊያን ጦር አገራችንን ለመወረር ሲመጣ ዶጋሌ ላይ በራስ አሉላ ጦር የተገደሉትን አምስት መቶ የጣሊያን ወታደሮች ለማስታወስ ነዉ። በ1877 ዓም ዘመናዊ መሳሪያ ታጥቆ ጦርና ጎራዴ በታጠቀዉ የራስ አሉላ ጦር ዉርደት የተከናነበዉ የጣሊያን ወራሪ ሠራዊት ብድሩን ለመመለስ በ1888 ዓ.ም ብዛት ያለዉ ካባድ መሳሪያ፤ መድፍና መትረየስ ታጥቆ አድዋ ድረስ ቢመጣም በዳግማዊ ሚኒሊክ የተመራዉ ጀግናዉ የኢትዮጵያ ሠራዊት እንደገና ዉርደት አከናንቦት በጥቁር ህዝብ ታሪክ ዉስጥ ትዝታዉ ምንግዜም የማይደበዝዝ ድል አስመዝግቧል። የኢትዮጵያ ሠራዊት ዶጋሌና አድዋ ላይ እስካፍንጫዉ የታጠቀዉን የጣሊያን ወራሪ ጦር ደጋግሞ ያሸነፈዉ በመሳሪያ በልጦ ወይም የተሻለ የዉትድርና ችሎታ ስለነበረዉ ሳይሆን ከወራሪዉ ጦር የበለጠ ቆራጥነትና የአለማ ጽናት ሰለነበረዉ ነዉ።
በሃያኛዉ መቶ ክፍለ ዘመን የተደረጉ ሌሎች የነጻነት ትግሎችን ስንመለከት በወቅቱ የአየር ኃይል ያልነበራት ትንሿ አገር ቬትናም በባህር፤ በአየርና በየብስ ጦርነት የገጠማትን ትልቁን የአለማችን ሀይል አሜሪካንን አሸንፋ ነፃነቷን ያስከበረችዉ በመሳሪያ ጋጋታ ሳይሆን የዛፍ ላይ ቅጠልና የተቦጫጨቀ ጨርቅ በለበሱ ነገር ግን ከፍተኛ የአላማ ጽናት በነበራቸዉ ጀግኖች ልጆቿ አማካይነት ነዉ።
አለማችን ትልቅ የጦርነት አዉድማ ናት ቢባል አባባሉ እምብዛም ከእዉነት የራቀ አባባል አይደለም። በእርግጥም አለም የጦርነት መድረክ ናት። ወደድንም ጠላን ወይም ብናምንም ባናምንም ጦርነቶች ሁሉ የተካሄዱት የህዝብን ነፃነት በሚደፍሩ ኃይሎችና መብቴንና ነጻነቴን አትንኩ በሚሉ ኃይሎች መካከል ነዉ። የአለማችን ታሪክ ወለል አድርጎ እንደሚያሳየን ደግሞ ይዋል ይደር እንጂ ሁሉም ዘለቄታዊ ድሎች የተመዘገቡት የአላማ ጽናት ባላቸዉ መብቴንና ነጻነቴን አትንኩ በሚሉ ኃይሎች ነዉ እንጂ የመሳሪያ ጋጋታ በተሸከሙ ኃይሎች አይደለም። የመሳሪያ ጋጋታ የተሸከመና ብዛት ያለዉ ወታደር ያሰለፈ ነገር ግን ለምን እንደሚዋጋ የማያዉቅና የአላማ ጽናት የሌለዉ ሠራዊት ግዜያዊ የጦር የጦር ሜዳ ድል ለያገኝ ይችላል፤ ሆኖም ጦርነቱን አሸንፎና የህዝብን ነጻነት ቀምቶ መዝለቅ በፍጹም አይችልም።
የአለም ታሪክ በነጭ ወረቀት ላይ በጥቁር ቀለም ቁልጭ አድርጎ የጻፈዉ አንድ ግዙፍ ሀቅ ቢኖር እልፍ ታንክና እልፍ አዕላፋት መድፎች ቢታጠቁም አምባገነኖች ለግዜዉ እንደተቆጣ ነብር ያስፈራሉ እንጂ ህዝባዊ አለማና ጽናት ያለዉ ጦር ፊት ሲቆሙ ፀሐይ እንደገላመጠዉ በረዶ ሟሽሸዉ የሚጠፉ ደንባራ ፈረሶች ናቸዉ። ለዚህም ነዉ ህዝብ አምባገነኖችን የወረቀት ላይ ነብር እያለ የሚጠራቸዉ።
ዛሬ ዕድሜዉ 35 እና ከዚያም በላይ የሆነ ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚኒልክን ቤ/መንግስት ተቆጣጥረዉ የረገጡትን፤ የገደሉትንና መብቱንና ነጻነቱን ገፍፈዉ ያዋረዱትን ሁለት የወረቀት ላይ ነብሮች ያስታዉሳል የሚል ሙሉ እምነት አለን። ደርግ በ1967 ዓም “ያለ ምንም ደም እንከኗ ይዉደም” እያለ ወደ ሥልጣን ሲመጣ በፊዉዳሉ ስርዐት ጀርባዉ የጎበጠዉን ኢትዮጵያዊ ሁሉ ደስ አሸኝቶ ነበር። እየቆየ ሲሄድና የተደበቀ ትክክለኛ መልኩ አደባባይ ሲወጣ ግን ያንን “ያለ ምንም ደም” የሚለዉን መፈክሩን ረስቶ ኢትዮጵያን የደም ገንዳ ሲያደርጋት በኢትዮጵያ ህዝብ ተጠልቶ አይንህን ለአፈር ተባለ። በሩሲያ ሰራሽ ዘመናዊ የጦር መሳሪያዎች አስካፍንጫዉ የታጠቀዉና በቁጥሩና በወታደራዊ ብቃቱ አፍሪካ ዉስጥ ትልቁን ሠራዊት የገነባዉ ደርግ “እንደ ዉኃ የሚያጥለቀልቅ ኃይል አለኝ” እያለ ቢፎክርም እሱ እራሱ ተጥለቅልቆና በያለበት ተሸንፎ አገራችን ኢትዮጵያን ለዘረኛ አምባገነኖች ያስረከበዉ ለእግሩ ጫማ ለወገቡ መታጠቂያ በሌለዉ የገበሬ ጦር ተሸንፎ ነዉ። ደርግ እንደታጠቀዉ መሳሪያ ብዛት፤ እንዳደራጀዉ ወታደራዊ ብቃትና እንደ ወታደራዊ መሪዎቹ ችሎታ ቢሆን ኖሮ ደርግን እንኳን ተዋግቶ ለማሸነፍ በዉግያ ለመግጠምም የሚያስብ ኃይል በፍጹም አይነሳም ነበር፤ ነገር ግን ድል ምን ግዜም ቢሆን የመሳሪያ ጋጋታ ዉጤት ሳይሆን የራዕይ ጥራትና የአላማ ጽናት ዉጤት በመሆኑ በወቅቱ ይህንን የተገነዘቡ ኃይሎች ህብረትና አገር ዉስጥ የተቀሰቀሰዉ ህዝባዊ ቁጣ አንድ ላይ ሆነዉ ደርግን ጠራርገዉ የታሪክ ቆሻሻ ዉስጥ ሊጨምሩት ችለዋል።
ዛሬ ደርግን አሸንፈዉ ደርግ የተቀመጠበት ወንበር ላይ የተቀመጡት ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የአገርን ኃብት ከመዝረፍ፤ የተቃወማቸዉን ከመግደልና የኢትዮጵያን አንድነት ከማፍረስ ዉጭ እንዴትና ለምን ደርግን የመሰለ ሠራዊት እንዳሸፉ የተገነዘቡ አይመስልም። ወያኔዎች ደርግ ከወደቀ ከ24 አመት በኋላ ዛሬም በየቀኑ ደርግን ቢኮንኑም ተቀምጠዉ አገር የሚገዙት ልበቢሱ ደርግ የተቀመጠበት ወንበር ላይ ነዉና የደርግ በሽታ ተጋብቶባቸዉ እነሱም እንደደርግ ልበቢሶች ሆነዋል።
ኢትዮጵያ በየዘመኑ እያደገና እየዘመነ የመጣ፤ ከተለያዩ የአገራችን ክፍሎች የተዉጣጣና ሞያን፤ ችሎታንና ወታደራዊ ሳይንስን አዳብሎ የታጠቀ ዘመናዊ የአገር መከላከያ ተቋም የነበራት አገር ነበረች። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች አዲስ አበባን ሲቆጣጠሩ ይህንን ዘመናዊ የአገርና የወገን መመኪያ የሆነ ሠራዊት አፍርሰዉና በየበረሃዉ ለእናት አገሩ የተዋደቀዉን ሰራዊት ለማኝ አድርገዉት ነዉ እነሱ ወርቃማዉ ዘር ብለዉ በሚጠሩት ዘር የበላይነት ላይ የተመሰረተ የመከላከያ ተቋም የገነቡት። ወያኔ የገነባዉ የመከላከያ ተቋም ባለፉት ሃያ አራት አመታት ዉስጥ አዲስ አበባ፤ ኦጋዴን፤ ጋምቤላ፤ ደቡብ ኦሞና በተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች የወሰዳቸዉን ፀረ ህዝብና ፀረ አገር እርምጃዎች ስንመለከት ተቋሙ እዉነትም ለአገር ጥበቃ ሳይሆን የወያኔን የበላይነት ለማረጋገጥ የተቋቋመ ኃይል መሆኑን በቀላሉ መረዳት ይችላል።
ይህ ሙሉ በሙሉ በትግርኛ ተናጋሪዎች የሚታዘዘዉ መከላከያ ሠራዊት ጋምቤላና ኦሞ ሸለቆ ዉስጥ ገበሬዉ ከቀዬዉ ተፈናቅሎ መሬቱ ባዕዳን ሲቸበቸብ አፉን ዘግቶ እንዲመለከት አድርጓል። ይሄዉ ሠራዊት በ1997 ዓም በአግአዚ ነብሰ ገዳዮች እየተመራ የህዘብ ድምጽ ይከበር ያሉ ከ200 በላይ ሠላማዊ ዜጎችን በግፍ ጨፍጭፏል፤ ከዚህ በተጨማሪ የወያኔ መከላከያ ሠራዊት አጋዴንና ጋምቤላ ዉስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል ፈጽሟል አሁንም እየፈጸመ ነዉ። እዚህ ላይ የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ትኩረት ሰጥቶ ሊመለከተዉ የሚገባዉ ነገር አለ፤ እሱም ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች ልማታዊ ሠራዊት ብለዉ እያሞካሹና “የመከላከያ ኃይሎች ቀን” የሚል ስያሜ ሰጥተዉ በየአመቱ ማክበር የጀመሩት በዐል የሚያወድሰዉ ይህንኑ አንድነቱንና ነፃነቱን እጠብቃለሁ ብሎ ቃል ኪዳን የገባለትን ህዝብ ያለ ርህራሄ የሚጨፈጭፈዉን የወያኔ ሠራዊት ነዉ። በተለይ ወያኔ ባለፈዉ ሳምንት ባህር ዳር ዉስጥ ያለ የለሌ የመሳሪያ ጋጋታዉን አደባባይ አዉጥቶ ለህዝብ እያሳየ ባከበረዉ የመከላከያ ቀን በዐል ለህዝብ ማስተላለፍ የፈለገዉ መልዕክት ቢኖር “ይህንን እያያችሁ ከወያኔ ጋር በእሳት አትጫወቱ “ የሚል የሞኝ መልዕክት ነዉ።
ይህ ባህር ዳር ላይ የተላለፈዉ መልዕክት ለማን እንደሆነና በተለይ ባህር ዳር የመልዕክቱ ማስተላለፊያ ቦታ ሆና የተመረጠችበት ምክንያት ለማንም ኢትዮጵያዊ ግልፅ ይመስለናል። የዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች መሰባሰቢያ የሆነዉ ህወሓት የተወለደዉም ሞቶ የሚቀበረዉም ሰሜን ኢትዮጵያ ዉስጥ መሆኑን እሱም ደጋፊዎቹም ካወቁ ቆይቷል። ዉቧና የጀግኖች መፍለቂያ የሆነችዉ ባህር ዳር ደግሞ ይህንን የወያኔን የቀብር ጉዞ ከጀመረች አመታት አስቆጥራለች። እንገዲህ ወያኔ በየቀኑ ከባድ መሳሪያና ስፍር ቁጥር የሌለዉ ወታደር ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ የሚያጓጉዘዉ ከዚሁ ከማይቀርለት ዉድቀቱ የሚያድኑት እየመሰለዉ ነዉ። እዚህ ላይ አንድ ወያኔ በፍጹም ያልተረዳዉ ነገር ቢኖር ህወሓትን ከኢትዮጵያ ምድር ጠራርጎ የሚያጠፋዉና ግብዐተ መሬቱን የሚፈጽመዉ ይሄዉ ወያኔ በነጋ በጠባ ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ የሚያጓጉዘዉ ሠራዊት መሆኑን አለመረዳቱ ነዉ። የወያኔ አይን ያወጣ ዘረኝነት በከፍተኛ ደረጃ ከተንጸባረቀባቸዉና በየቀኑ በዘረኝነት እሳት ከሚለበለቡ የህብረተሰብ ክፍሎች ዉስጥ አንዱና ዋነኛዉ የመከላከያ ሠራዊት ነዉ። ይህ ሰራዊት እንደ መሬት የሚረግጡትን የወያኔን አለቆቹን ትዕዛዝ ተቀብሎ ከታሰረበት የዘረኝነት እስር ቤት ነፃ ሊያወጡት በሚታገሉ የኢትዮጵያ ህዝብ የነጻነት ኃይሎች ላይ መሳሪያዉን ያዞራል ብሎ የሚያምን ኢትዮጵያዊ ያለ አይስለንም፤ በሌላ በኩል ደግሞ የወያኔን የመሳሪያ ጋጋታ አይቶ ለእናት አገሩ አንድነትና ለኢትዮጵያዉያን ወገኖቹ ነጻነት ህይወቱን ከመስጠት ወደ ኋላ የሚል ኢትዮጵያዊ ቢኖር እሱ ከወያኔ ጋር በጥቅም የተጋባ ከሃዲ መሆን አለበት። የኢትዮጵያ ህዝብ ምንግዜም ቢሆን በወሬ ቱማታና በመሳሪያ ጋጋታ ትጥቁን ፈትቶ አያዉቅም። በ1930ዎቹ ፋሺስት ጣሊያኖችንና በ1970ዎቹ ወታደራዊዉን ደርግ ተዋግቶ ያሸነፈዉ እነዚህ ኃይሎች የታጠቁትን መሳሪያ እየቀማ በተዋጋቸዉ ነጻነት የጠማዉ ኃይል ነዉ። የዛሬዎቹ የወያኔ ፋሺስቶች እጣም ጣሊያንና ደርግ ከገጠማቸዉ ሽንፈት የተለየ አይሆንም።
የአገራቸዉን የኢትዮጵያን ዳር ድንበር ከጠላት ለመከላከል የመከላከያ ሠራዊትን የተቀላቀሉ የኢትዮጵያ ልጆች “ዶሮን ሲያታልሏት በመጫኛ ጣሏት” የሚለዉን የአባቶቻቸዉ ምሳሌያዊ አባባል ምንነት በሚገባ የሚረዱ ይመስለናል። ስለሆነም ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ በዘር ለይቶ እየረገጣቸዉ፤ እያዋረዳቸዉና ከሰዉ በታች አድርጎ እየተመለከታቸዉ ይህንን ቅጥ ያጣ በደል ለማረሳሳት የመከላከያ ቀን እያለ በሚያከብረዉን የይስሙላ በዐል እንድም የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባል ሊታለል አይገባም። ከአግአዚ ነብሰ ገዳዮች ዉጭ ያለዉ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እንደማንኛዉም የወያኔ እስረኛ እንደሆነ የህብረተሰብ ክፍል ነፃ መዉጣት የሚገባዉ ክፍል ነዉ። ይህ የህዝብ ወገን የሆነዉ የመከላከያ ሠራዊት እራሱን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያዉያን ወንድሞቹንና እህቶቹን ጭምር ከወያኔ ዘረኝነት ነጻ ሚያወጣት አለበት። እስከቅርብ ግዜ ድረስ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት ብዙም አማራጭ ስላልነበራቸዉ አንገታቸዉን ደፍተዉ የጠላታቸዉን የወያኔን ትዕዛዝ እየተቀበሉ ሲፈጽሙ ቆይተዋል፤ አሁን ግን አንገታቸዉን ቀና አድርገዉ የወያኔን አንገት የሚያሰደፉበት አመቺ ሁኔታ ተፈጥሮላቸዋል። ዛሬ ለእናት አገራቸዉ ነጻነት በህይወታቸዉ ቆርጠዉ ብረት ያነሱ የነጻነት አርበኞች የመከላከያ ሠራዊት የወያኔ አለቆቼን ትዕዛዝ ላለመቀበልም ሆነ ወይም የታጠቀዉን መሳሪያ ወደ ጠላቱ ወደ ወያኔ ማዞር የሚችልበትን አመቺ ሁኔታ ፈጥረዉለታል።
ዉድ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት ሆይ ጨለማዉ ሊጠራ ሲል ይበልጥ ይጨልማልና ወያኔ ወደ ሰሜናዊዉ የአገራችን ክፍል የሚያጓጉዘዉ የመሳሪያ ጋጋታና የሠራዊት ብዛት በፍጹም ልትደናገጥ አይገባም። ወያኔን ካንተ በላይ በቅርብ የሚያዉቀዉ የለም፤ የወያኔ ኃይለኝነትና ትልቅ መስሎ መታየት አንተ በዉስጡ ስላለህበት ብቻ ነዉ። ስለዚህ ይህንን ፀረ ኢትዮጵያ ኃይል ለቅቀህ በያለህበት ላንተ፤ ለወገኖችህና ለእናት አገርህ ነፃነት መከበር ከቆረጡ ወገኖችህ ጋር በፍጥነት ተቀላቀል። ይህንን ማድረግ የማትችለዉ ደግሞ ወያኔ ከገዛ ወገኖችህ ጋር እንድትዋጋ ትዕዛዝ ሲሰጥህ የታጠከዉን መሳሪያ ወደ ወገኖችህ ሳይሆን ወደ ራሱ ወደ ወያኔ አዙር። ወያኔ ለትንሽ ግዜ የማይበገር መስሎ ሊታይ ይችል ይሆናል የማይቀረዉ የዘለቄታ ድል ግን ምን ግዜም የህዝብ ነዉ፤ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ደግሞ ትናንት አንደነበረ ሁሉ ዛሬም የኢትዮጵያ ህዝብ አለኝታ ነዉ።
ድል የህዝብ ነዉ!
source www.ginbot7.org

Saturday, February 21, 2015

የዛሬ የቂሊንጦ አጭር ቆይታ አብርሃን መጠየቅ ከጀርባ ሰው ያስከትላል (ከኤልያስ ገብሩ ጎዳና )

‹‹ዕድሜያችንን መቼ ሰራንበት፣ ልደት ማክበርም ያስፈራኛል፡፡
እንኳን ተወለድክ ላላችሁኝ በሙሉ ከልብ አመሰግናለሁ››
ጦማሪ እና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ኃይሉ
ከዛሬ ከሰዓት በኋላ ከወዳጄ አቤል አለማየሁ ጋር ወደ ቂሊንጦ እስር ቤት አምርተን ነበር፡፡ አካሄዳችን በዞን ሁለት የሚገኙትን አብርሃ ደስታን፣ ጦማሪ እና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ኃይሉንና ጦማሪ አጥናፍ ብርሃንን ለመጠየቅ ነው፡፡
የቃሊቲ እና የቂሊንጦ ጸሐይ ከረር ያለች ብትሆንም በቦታው ደርሰን ወደፖሊሶች ለምዝገባ ተጠጋን፡፡ ጠያቂና ተጠያቂ መዝጋቢ የሆነችው ሴት ፖሊስ ‹‹ማንን ነው የምትጠይቀው?›› ብላ አቤልን ጠየቀችው፡፡ በፍቃዱን እና አጥናፍን መሆንኑ ነገራት፡፡ መዘገበችውና ሂድ አለችው፡፡ ‹‹አንተስ ማንን ነው?›› ስትል ጠየቀችኝ፤ ‹‹አብርሃ ደስታን›› አልኳት፡፡ ቀና ብላ አየችኝና ‹‹ቆይ፣ ቁጭ በል›› የሚል መልስ መለሰች፡፡ ሌሎች ሰዎችን መመዝገቧን ቀጠለች፡፡ ‹‹ሰዓት እየሄደ ነው፣ ችግር አለ ወይ?›› አልኳት፡፡ ‹‹አይ ችግር የለም›› ካለች ከተወሰኑ ደቂቃዎች በኋላ ሌላ መዝገብ አምጥታ ፓስፖርቴን መዘገበችው፡፡ (መታወቂያዬ አልታደሰም) ከመዘገበች በኋላም ሌላ የፎርም መሙያ አውጥጣ በድጋሚ መዘገበች፡፡ ይሄንን ስትመዘግብ እኔ እንዳይባት ስላልፈለገች ስትደብቀው አስተውያታለሁ፡፡ …ከሌላ ወንድ ፖሊስ ጋር ከተነጋገረች በኋላ ግባ አለችኝ፡፡Elias Gibru
የጸሐይ መነጽር ማውለቅ ግድ ነበር፡፡ ያው ፍተሻውን አልፌ ወደዞን ሁለት አመራሁ፡፡ ከኋላዬ አንድ ሲቪል የለበሰ ወንድ በቅርብ ርቀት እየተከተለኝ ነበር፡፡ አብርሃን አስጠራሁት፡፡ ከኋላዬ የሚከተለኝ ሰው ከጎኔ ሆኖ ሌሎች ጠያቂዎችን ለመጠየቅ ማስመሰል ሞከረ፡፡ በውስጤ ፈገግ መጣ፡፡
አስተናባሪዎቹ ‹‹አብርሃ እዚህ የለም፤ የዞን ሁለት መጠየቂያ ተቀይሯል›› አሉኝ፡፡ በእርግጥም ዞን አንድ ታስሬ በነበረበት ጊዜ የማውቃቸውን እስረኞች ተመለከትኳቸውና ሰላም ተባባልን፡፡ ልወጣ ስል ኡስታዝ አቡበከር አሕመድ በርቀት አይቶኝ ሰላም አለኝ፡፡ በደስታ ሰላም አልኩት፡፡ ነገር ግን ተመልሼ በእጄ ሰላም እንዳልለው ያ ከጀርባዬ ያለ ሰው ነበር፡፡ ከዚህ ቀደምም ‹‹አቡበከርን ለምን ጠየከው?›› ተብዬ የተፈጠረውን ግርግር አስታወስኩኝ፡፡ አብበከርም ይሄ ስለገባው በርቀት ሰላም ብሎኝ በእጁ ሂድ አለኝ፡፡
የዞን አንድ መጠየቂያ ለዞን ሁለት ታሳሪዎች፤ የዞን ሁለት ደግሞ ለዞን አንድ ታሳሪዎች መጠየቂያ ሆኗል፡፡ አቤል በፍቄንና አጥናፍን አስጠርቷል፡፡ እኔም አብርሃን አስጠራሁ፡፡ በፍቄና አጥናፍ ወዲያው መጡ፡፡
ያ ከጀርባዬ የነበረ ሲቪል ኮፍያ ለባሽ ከጎኔ ቆሟል፡፡ ለአጥነፍ ‹‹በቃ እናንተ ከአቤል ጋር አውሩ፡፡ እኔ አብርሃን ስላጠራሁ ልጠብቀው፡፡ ከአንድ ሰው በላይ መጠየቅ አይቻልም ብለዋል›› አልኩት፡፡ አጥናፍ ከዚህ ቀደም የደረሰብኝን አስታውሶ ‹‹አብርሃ አሁን ጠበቃ ተማንን ሊያገኝ ሄዷል፤ ከጎንህ የቆመው የግቢው ደህንነት ነው፡፡ ይሄን ንገረውና እስከዚያው ከእኛ ጋር ሁን›› አለኝ፡፡ ያን ሰውዬ ትከሻውን ስነካው ደንገጥ ብሎ ዞር አለ፡፡ ስለሁኔታው ነገርኩት፡፡ ‹‹እሱ (አብርሃ) እስኪመጣ ብቻህን ተቀምጠህ ጠብቅ›› አለኝ፡፡ ‹‹እስኪዚያ እነሱን ላናግራቸው›› አልኩት፡፡ ‹‹ብቻህን ብትቀመጥ ይሻልሃል አለኝ›› ተናድጄ ወደውጪ ወጥቼ ሌሎች ፖሊሶችን ስለሁኔታው አስረዳኋቸው፡፡ ኃላፊነት የሚወስድ ጠፋ፡፡ በመጨረሻም አንዱ ፖሊስ ‹‹እሱ አስኪመጣ ውስጥ ጠብቀው›› የሚል ምላሽ ሰጠኝ፡፡ የመጣው ይምጣ በሚል ገብቼ ከበፍቄ ጋር ማውራት ጀመርኩ፡፡
‹‹በፍቄ እንኳን ተወለድክ›› አልኩት፡፡ አሜን ካለኝ በኋላ ‹‹ዕድሜያችንን መቼ ሰራንበት፡፡ ልደት አክብሬ አላውቅም፡፡ ልደት ማክበርም ያስፈራኛል፡፡ ግን እንኳን ተወለድክ ላላችሁኝ በሙሉ ከልብ አመሰግናለሁ›› ሲል እየሳቀ መለሰልኝ፡፡
አቤል እና አጥናፍ ጋር የጦፈ ጨዋታ ይዘዋል፡፡ እኔም ከበፍቄ ጋር ባለችን አጭር ደቂቃ ስለሀገር ጉዳይ፣ ስለዘንድሮ ምርጫ፣ ስለአልጀዚራ ዘስትሪም የሰሞኑ ዘገባ፣ ስለ ክሳቸው እና እስራቸው ጉዳይ፣ ስለእኔ የክስ ሁኔታ፣ በአንድነት ፓርቲ ስለደረሰው ሁነትና አደጋ …በጥቂቱ አወጋን፡፡የመለያያ ደወል ተደወለ፡፡ አብርሃም ሳይመጣ ቀረ፡፡ ያው፣ ቻው ብሎ መለያየት ግድ ነበርና ተለያየን!!!
Source ecadforum.com

Wednesday, February 18, 2015

Ethiopia's Media War: Al Jazeera, The Stream


 repression.Ethiopia's jailed Zone 9 bloggers are on trial this week for terrorism and treason, charges facing more than two dozen journalists, bloggers and publishers. To avoid arrest, 30 journalists fled the country in the past year. The government says they’re criminals, destabilising Ethiopia's fragile democracy in the name of “press freedom.”Rights groups  say they’re victims of repression.


Saturday, February 14, 2015

የ2007ቱን ሀገራዊ ምርጫ ሂደት እና ከምርጫዉ ዉጭ ያሉ አዋጭ አማራጮችን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የአቋም መግለጫ

አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሰላማዊ፣ ተዓማኒና ፍትሀዊ በሆነ ምርጫ የማይፈልጋቸውን መሪዎች መሻር፤ የሚፈልጋቸውን ደግሞ መሾም የሚያስችሉትን መሠረቶች ለመጣል የሚታገል ንቅናቄ ነው። እንደሚታወቀው የሕዝብ እውነተኛ ፍላጎት የሚገለጽበት እውነተኛ ምርጫ እንዲኖር ገለልተኛና ቀልጣፋ የፍትህ ሥርዓት፣ የጦርና የፓሊስ ሠራዊት ሊኖሩ ይገባል። ነፃ የሚዲያ ተቋማትና በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የሲቪክ ማኅበራት መኖርም መታለፍ የሌለባቸው አቢይ ጉዳዮች ናቸው። አማራጭ ፓሊሲዎችን ማቅረብ የሚችሉ በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የፓለቲካ ፓርቲዎች ከሌሉም አማራጮች የሉምና ምርጫ ትርጉም የለውም። ይህ ሁሉ ቢሟላ እንኳን ምርጫውን የሚያስፈጽመው አካል ገለልተኛ፣ ሀቀኛና ተዓማኒ ካልሆነ የሚደረገው ምርጫ የመራጩን ሕዝብ ፍላጎት የሚያንፀባርቅ ሊሆን አይችልም።
ከላይ የተዘረዘሩትን የምርጫ እሴቶች ሙሉ በሙሉ ባይሆንም እንኳን የተወሰኑትን በመጠኑም ቢሆን ያካተተ ምርጫ እንዲኖር መጣርና በሂደት የምርጫውን አፈፃፀም ማሻሻል ይቻል ይሆናል በሚል እምነት የዲሞክራሲ ኃይሎች በህወሓት የሴራ ምርጫዎች ሲሳተፉ ቆይተዋል። ሆኖም በህወሓትና በእውነተኛ ምርጫ መካከል ያለው ተቃርኖ እያደር እየሰፋ ሲሄድ እንጂ ሲጠብ አልታየም። በህወሓት ሙሉ ቁጥጥር ስር በሚካሄድ ምርጫ ኢትዮጵያን የሚጠቅም ለውጥ ሊመጣ ይችላል የሚለው እምነት ለአርበኞች ግንቦት 7 ፈጽሞ የተሟጠጠው ከምርጫ 97 ማግስት ጀምሮ ነው። በግንቦት 7 ቀን 1997 ዓም የኢትዮጵያ ሕዝብ በታላቅ የለውጥ ተስፋ የሰጠው ድምጽ በህወሓት የተዘረፈው ከላይ የተዘረዘሩት ተቋማት ያልነበሩ በመሆናቸው፤ ስለዚህም ከምርጫ በፊት ተቋማቱን መገንባት፤ ተቋማቱን ለመገንባት ደግሞ ህወሓትን ከስልጣን ማስወገድ ይገባል ብሎ በማመኑ ነው አርበኞች ግንቦት 7 በሁለገብ የትግል ስልት በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኘው።
ያም ሆኖ ግን በምርጫ ላይ ያላቸው ተስፋ ፈጽሞ ያልተሟጠጠ ፓርቲዎችን በማክበርና ሥራቸውንም አስቸጋሪ ላለማድረግ ሲባል ከምርጫ 97 ወዲህ የነበሩ ብሄራዊም ሆነ ክልላዊ ምርጫዎችን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምርጫ ዉጭ ያሉ ሌሎች አማራጮችን ብቻ እንዲመለከት አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ አድርጎ አያውቅም ነበር። አሁን ግን የአገራችን ኢትዮጵያ የፓለቲካ ሁኔታዎች ይህንን የቆየ አቋም በሚያስቀይር መንገድ፤ የአገራችንን የወደፊት ዕድል ብቻ ሳይሆን ባጠቃላይ ያካባቢውን ሰላም በሚጎዳ መልኩ ተቀይሯል። የሰሞኑ የወያኔ እርምጃዎች ትንሽ ተስፋ ያደርግ የነበረውን የዴሞክራሲ ወገንተኛ ተስፋም እምሽክ አድርጎ በልቶታል:: እየተቃረበ ያለው ዓይነት የፌዝ ምርጫ ወያኔ እንደ እንጄራ የራበውን የተቀባይነት እጦት ለአጭር ጊዜ ያስታግስለት ይሆናል እንጂ የሀገሪቱን እያደር እየተወሳሰበ የመጣ ችግር ለጊዜውም እንኳን የሚያስታግስ አይሆንም፤ ይልቁንም ጊዜው በገፋ ቁጥር ችግሩ መቋጠሪያ የጠፋው እየሆነ ይሄዳል::
የሁኔታውን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባት የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራር የወቅቱን የአገራችን የፓለቲካ ሁኔታ በጥንቃቄ መርምሮ የሚከተሉት ግንዛቤዎች ላይ ደርሷል።
1. ህወሓት ብዙዎች እትዮጵያዊያን የተሰውላቸውን አንድነት ፓርቲንና መኢአድን በመበተን የድርጅቶቹን ስምና ንብረት ለአገልጋዮቹ መስጠቱ፤ ከዚህ በፊት ሲያደርግ እንደነበረው የመራጭን ድምጽ መስረቅ ሳይበቃው የምርጫ ተወዳዳሪንም መዝረፍ መጀመሩን አመላካች ነው። ይህ ተግባር ህወሓት የምርጫ ውጤትን ብቻ ሳይሆን ተወዳዳሪዎችንም እሱ ራሱ ለመምረጥ መወሰኑን ያሳያል፤ ከዚህ በተጨማሪ የሴራ ምርጫውን ከጅምሩ ጀምሮ አስቀድሞ እስከተወሰነለት መዳረሻው ድረስ ለምንም ዓይነት ያልተጠበቀ አጋጣሚ (በምርጫው ወቅት የሚደረጉትን ክርክር ተብዬዎች ጨምሮ) እድል ላለመስጠት ወስኖ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን በግልጽ ያሳያል፤
2. ይህ እኩይ ውሳኔ በምርጫ ቦርድ ፊርማና አንደበት ቢነገርም ምንጩ የህወሓት ፓሊት ቢሮ መሆኑን የሚከተሉት ተግባራት ይጠቁማሉ፤
2.1. በምርጫ ቦርድ በኩል እንዲገለጽ የተወሰነው እርምጃ ለማስመሰል ያክልም ቢሆን የህጋዊነት ሽፋን እንዲኖረው አለመደረጉ ውሳኔው ፍጹም እብሪተኛ በሆነ አካል መወሰኑን ያመለክታል። እንዲህ ዓይነቱ እብሪተኛ አካል ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ነው። ውሳኔውን ለማስፈፀም የነበረው ጥድፊያም ይህንኑ ያጠናክራል።
2.2. ለማስመሰያ ያክል እንኳን ምንም አይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሳይኖር ፓሊስ የአንድነትና የመኢአድ ቢሮዎችን መውረሩ፤ ህወሓት አንድነትንና መኢአድን አጥፍቶ የድርጅቶቹን ስሞችና ንብረቶች ለሚፈልጋቸው ሰዎች ሰጥቶ በአስቸኳይ ለምርጫ ድራማው በፊት መስመር ሊያሰልፋቸው መወሰኑን አመላካች ነው። እንዲህ ዓይነት ከባድ ውሳኔ የሚሰጠው ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ብቻ ነው።
2.3. ወደ ፈቃድ መንጠቅ ከመደረሱ በፊትም በሰማያዊ ፓርቲ፣ በአንድነትና በመኢአድ አባላት የደረሰው አረመኔያዊ ድብደባ፤ ንቁ የፓለቲካ ተሳትፎ የሚያደርጉ ዜጎች ላይ የሚደርሰው እስር፣ መሰወርና እና ባልታወቁ ሰዎች ተገድሎ መገኘት መብዛት እነዚህን አገራዊ ፓርቲዎች የመበተን የፓለቲካ ውሳኔ መሰጠቱን አመላካቾች ናቸው።
3. ለጊዜው የፈቃድ ነጠቃና የንብረት ዘረፋ የተፈፀመው በአንድነትና በመኢአድ ላይ ቢሆንም በሰማያዊ ፓርቲ ላይ በየእለቱ እየጠነከረ የመጣው የአፈና እርምጃም በተመሳሳይ ፓርቲውን ወደማገድ አለዚያም ፈጽሞ መንቀሳቀስ ወደማይችልበት ደረጃ ሊያደርሰው ይችላል የሚል እምነት አሳድሯል። ሌሎች ፓርቲዎችም ከዚህ ህወሓት ካሰመረው የውሸት ጫወታ መስመር የመውጣት ዝንባሌ ቢያሳዩ ተመሳሳይ እርምጃ አይቀርላቸውም።
4. የህወሓት የወቅቱ የጥፋት ዒላማ ያነጣጠረው አንፃራዊ በሆነ መንገድ የተሻለ መዋቅርና ማኅበራዊ መሠረት ባላቸው እና በአገራዊ አጀንዳዎቻቸው በሚታወቁ ፓርቲዎች ላይ መሆኑ፤ የወቅቱ የጥፋት ዘመቻ የኢትዮጵያ አንድነትን የማዳከምና ከፋፍሎ የመግዛት የህወሓት ትልቁ አጀንዳ አካል መሆኑን ያሳያል።
5. እራሱን በዘር ያደራጀዉና ኢትዮጰያ ዉስጥ ያለዉ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ አደረጃጀት ከዚሁ እሱ ከተደራጀበት የዘር አደረጃጀት ዉጭ እንዲሆን በፍጹም የማይፈቅደዉ የወያኔ አገዛዝ፤ መጣፊያው ሲያጥረውና ወደ ማይቀረው ውድቀቱ ሲያመራ፤ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል እንዳለችው አህያ አገራችን ኢትዮጵያን በቀላሉ ወደማትወጣዉ የዘዉግ ግጭት ዉስጥ አስገብቶ ዘመናት ያስቆጠረዉ አንድነቷ እንዲፈረስ በትጋት እየሠራ መሆኑን ያሳያል።
6. ከመለስ ዜናዊ ሞት ወዲህ ህወሓት ከሁሉን ጠቅላይ (totalitarian) አገዛዝ ወደ ፋሽስታዊ ቡድንነት ያሽቆለቆለ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ህወሓት ዘረኛ፣ ጠቅላይና ፈላጭ ቆራጭ ጨቌኝ በመሆኑ ፋሽስት ብለነዋል። ሆኖም በታሪክ የሚታወቁ ፋሺስታዊ አገዛዞች ከፍተኛ ብሄራዊ ስሜት የነበራቸው ሲሆን የህወሓት ፋሽስታዊ አገዛዝ ግን ብሔራው ስሜት አልባ መሆኑ ልዩ እና የበለጠ አደገኛ ያደርገዋል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን የህወሓት መሪዎችንና ጥቂት ሌሎች አጫፋሪዎቻቸውን የያዘ ለጊዜው አስተባባሪ መሪ የሌለው ሆኖም ግን የጦር ሠራዊትን፣ የስለላ መዋቅሩንና ፓሊስን ተቆጣጥሮ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያን እየገዛ ያለው ይህ አስኳል የለሽ ፋሽስታዊ ቡድን መሆኑ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን ተደላድሎ መሪ እንዲፈጥር ከተፈቀደለት አገራችንን የከፋ መከራ ውስጥ ሊከታት እንደሚችል ግንዛቤ ተወስዷል።
ከላይ በአጭሩ ከተራ ቁጥ 1 እስከ 6 የተዘረዘሩትን በማገናዘብ በግንቦት 2007 ሊደረግ የታቀደውን አምስተኛው ዙር ሀገር አቀፍ የሴራ ምርጫን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7 አመራር ውሳኔዎችን አስተላልፎ ከዚህ የሚከተሉት ጥሪዎችን ለኢትዮጵያ ሕዝብ አቅርቧል።
1. በምርጫ 2007 መሳተፍ ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ ሁኔታዎችን ከማመቻቸት ይልቅ ፋሽስታዊውን ቡድን የሚያጠናክርና የኢትዮጵያን ሕዝብ የወደፊት ዕድል የሚገድል በመሆኑ፣ ለፍትህ፣ ለነፃነት፤ ለዲሞክራሲና ለአገር አንድነት ግድ ያላቸው ወገኖች ሁሉ ከአሁኑ ከዚህ የይስሙላ ምርጫ ዉጭ ዓይኖቻቸውንና ሙሉ ጉልበታቸዉን በሌሎች የኢትዮጵያን ሕዝብ ነፃነት በሚያፋጥኑ አማራጮች ላይ እንዲያሳርፉ ጥሪ ያደርጋል። አርበኞች ግንቦት 7 የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዚህ ዓይን ያወጣ የሴራ ምርጫ ይልቅ መብቱን፤ ነፃነቱንና እኩልነቱን በሚያፋጥኑለት በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመፅ የትግል አመራጮች ላይ እንዲሳትፍ ለመላው ያገሪቱ ሕዝብ ጥሪ ያስተላልፋል። ህወሓት ማኅበረሰባችንን ለመከፋፈልና ለማባላት የሚያደርገውን እኩይ ሴራ በጋራ እንድናከሽፈው ወገናዊ ጥሪ ያስተላልፋል፤ “አንከፋፈልም፤ ተከፋፍለንም አንጠቃም“ እንበል ይላል::
2. ህወሓትን ማስወገድ የሚቻለው በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ በመሆኑ፤ ከሁለቱ አንዱንም አለመያዝ ሌላ ሰው ታግሎ ነፃነቴን ያቀዳጀኝ እንደማለት የሚቆጠር በመሆኑ፤ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በአፋጣኝ ከእነዚህ ሁለት የትግል ዘርፎች ዉስጥ የተሻለ አስተዋጽኦ አበረክታለሁ በሚለው የትግል ዘርፍ ውስጥ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጥሪ ያቀርባል።
3. አርበኞች ግንቦት 7፣ በሁለቱም የትግል ዘርፎች ድርጅታዊ መዋቅሩን እያሰፋና ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በመተባበር በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ ህወሓትን ከስልጣን ለማስወገድ አቅዶ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ኢትዮጵያዊያን በስፋት እንዲቀላቀሉት፤ በኅብረት እንድንቆም እና የህወሓትን ውድቀትና የኢትዮጵያን ትንሳኤ እንድናፋጥን ጥሪ ያደርጋል::
4. ያለንን አቅም በሙሉ ህወሓትን በማስወገድ ላይ ካዋልነው አንድ ጠንክር ያለ ሕዝባዊ አመጽ አገዛዙን ሊያፍረክርክው የሚችል በመሆኑ፤ በአንድ ወይም በሌላ መንገድ ከምርጫ ጋር ለተያያዙ ሥራዎች ሊውል ታስቦ የነበረው የሰው ኃይል፣ ጊዜ፣ ገንዘብና እውቀት ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀሻነት እንዲውል ጥሪ ያደርጋል።
5. በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንም በ2007 ምርጫ ላይ ጊዜና ንብረት ከማባከን ይልቅ በአንድ ልብ በኢትዮጵያ ውስጥ ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀስ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ ጥሪ ያደርጋል። ከሁሉም ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች የተውጣጣ አካል የዚህን ጥሪ ተፈፃሚነት እንዲከታተል ቢደረግ ይበልጥ ውጤታማ ይሆናል ብሎ ያምናል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ
ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ
source www.ginbot7.org